Friday, December 25, 2009

ዳኛው ውሳኔ ሰጠ ቁጥር ፮

ከሁሉም በማስቀደም እንኴን ለፈረንጆች ገና አደረሳችሁ እያለ መረዋ ልባዊ ምኞቱን ይገልጻል።

በቤተክርስቲያናችን እየተፈጠረ ያለውን መከፋፈል በመመልከት በመረዋ መጽሔት በተደጋጋሚ አሸናፊ አይኖርም ብለን መናገራችን ይታወሳል። ዛሬም ዳኛው ሕጉን የመቀየር መብት ቦርዱ በመተዳደሪያ ደንቡ አንቀጽ 11.2 መሰረት አለው ብሎ ከተከሳሽ ጠበቆች ጋር መስማማቱን ይፋ ያደረገው ማክሰኞ እለት መሆኑን ለመስማት ችለናል። ባለፈው እንደነገርናችሁ ዳኛው የቦርድ አባላትን ሲናገር "ይህንን የምታደርጉት አባላትን ከቤተክርስቲያኑ ለማባረር፤ በስልጣናችሁ በመጠቀም አባላትን አስገብራችሁ ለመሰንበት፤ ቤተክርስቲያኑን በጥቂት ግለሰቦች እጅ አስገብቶ ፈላጭና ቆራጭ ሆኖ ለመቀጠል ነው።" ያለውን እንደ ምክር ቦርዱ የወሰደው አልመሰለንም። "ተስማምቶ ልጅ መውለድ እያለ በጉልበት ደፍሮ ማስረገዝ " የተለያዩ መሆናቸውን እንዳለማወቅ አይነት መሆኑ ነው። በሚመጣው እሁድ የአስተዳደሩ ቦርድ ወንድሞቼ አሸነፍን እንደሚልና ደሰተኛ መሆኑን በደጋፊዎች እልልታና ጭብጨባ ለማሳጀብ እንደተነሳ እወቁ ብለን ያናገርናቸው ከሳሾች ያሉን ነገር ቢኖር ከሳምንት በኋላ ደግሞ እንደለመዱት ተከሰናል እንደሚሉ በእርግጠኝነት ልንነግራችሁ እንወዳለን የሚል ነበር። ከአባባሉ እንደተረዳነው ክሱ ከትላንትናው በከፋ መልክ እየቀጠለ መሆኑን ነው። ወንድሞችና እህቶች ቀደም ብለን አሸናፊ አይኖርም ያልናችሁ ለዚሁ ነበር። የተናገርነው እውነታው እየታየ ነው። በመሃከሉ የሰማንው ጥሩ ወሬ ቢኖር ተጣልተው የነበሩት የቦርድ አባላት በሽማግሌ የመታረቃቸው ዜና ነው። የነሱ መታረቅ ጥሩ ሆኖ እያለ "ከከሰሱን ጋር አናወራም" ማለታቸው ግን እየገረመን እየመጣ ነው። ለጠበቃ ያወጣንውን እናስከፍላለን ብለው ቢነሱም ዳኛው አታስከፍሉም ስላለና ስለወሰነ መናደዳቸውን በየቦታው እየዞሩ የሚናገሩት የቦርድ አባላት በሁለቱም ወገን የሚጠፋው ገንዘብ የዚሁ የቤተክርስቲያን አባላት ንብረት መሆኑንን ሊገነዘቡ አለመቻላቸው ይደንቀናል። በነሱ ወገን አላግባብ ገንዘብ ማባከንም ተመልሶ በግለሰብ ሊያስጠይቅ እንደሚችል ማወቅም ይኖርባቸዋል። ማንም ይሁን ማን በቤተክርስቲያን ጉዳይ ቂም ይዞ ባይሄድ ጥሩ ነው። የቦርድ አባላት ከሳሾቹ የሂትለሩ የናዚ ፋሺስት ፓርቲ የወጣት ማህበር አባላት አይነት ናቸው ብለው በመሃላ ለፍርድ ቤት ቃላቸውን ሲሰጡ ማፈር ነበረባቸው። ወንድሞችና እህቶች በሚሊዮን የሚቆጠር ሕዝብ የጨረሰውን ናዚን ከወንድሞችና ከእህቶት ክርስቲያኖች ጋር ማመሳሰል ወንጀል ነው። ብልግና ነው። ቦርዱ አዲስ ኮሚቴ አቌቁሞ ሕጉን እንደገና ለማሻሻል እያስጠና መሆኑን እንደኛ ሰምታችሁ ይሆናል። ባለፈው የተቀየረው እንዳስፈራን የዛሬው ምን ይዞ ይመጣ ይሆን ብለን መፍራታችን አልቀረም። ፍራቻቸን ለሌላ ክስ መነሻ መንደርደሪያ ወይም ማጠናከሪያ ይሆናል እንጂ በተያዘው መልክ መቀጠሉ ጥቅም የለውም ብለን ስላመንን ነው።


የቦርድ አባላትም ሆኑ ካሳሾች ሊገነዘቡት የሚገባው ነገር ቢኖር። ይህ የቤተክርስቲያን ጉዳይ መሆኑንና በቤተክርስቲያን ጉዳይ ደግሞ ስልጣን የሚኖረው የመንፈሳዊ አባቶች መሆኑናቸውን ነው። ለነገሩ ይህንን ቦርዱ የያዘው መንገድ መሆኑንና መከራከሪያውም እሱ እንደሆነ የተቀበል ለመሆኑ "ይህ ጉዳይ በሲኖዶስ በኦርቶዶክስ እምነት መፈታት ያለበት እንጂ በፍርድ ቤት መሆን የለበትም" ብሎ በመከራከሩ ሌላ አዲስ የማስታረቂያ መንገድም እንደከፈተ መታወቅ አለበት እንላለን። ሁላችንም ቦርዱ እንዳለው ሁሉ በሲኖዶሱ ማመንና የሲኖዶሱን ሕግ መቀበል ይኖርብናልና።


በነገራችን ላይ ልብ ብላችሁ መተዳደሪ ደንቡን ብታነቡት ይኸው የሚያጣላው የሕግ አንቀጽ 11.1 ላይ " ......... የኢትዮጵ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያንን ሕግና ስርዓት ተከትሎ" ደንቡ መሻሻል እንደሚችል ያሳስባል። ምን ማለት ነው? ለአንባብያን እንተወው። በየወሩ ሕግ ከማሻሻል ይልቅ ተሰብሰቦ በመወያየት የችግሮችን መንሰኤ አውቆ የማያዳግም መልስ መስጠት ይበጃል ብለን አሁንም ስለምናምን ልባችንን ሰፊ ብናደርግና ለሰላም ብንነሳ መልካም ነው። ክሱን አሸነፍን ብለው የተደሰቱ ካሉ የተከፉትን አለማጤን ይሆናል። ክርስቲያን ደግሞ ወንድሙ ሲበሳጭ የሚደሰት አይደለምና። ከሳሾች ክስ የመሰረቱት "እምነት ብለው ሳይሆን የመብት እረገጣ ሲበዛ፤ ቦርዱ ፈላጭ ቆራጭ ሆኖ አንጋፋዎቹን እየገፋ የማናውቃቸውን አዲስ መጤዎች በማስገባት ስለበጠበጠን። ቦርዱ አስተዳደርን አልፎ የመንፈሳዊ አባት ሊሆን ሲሞክር፡ ክርስትና የሚያነሱትን ማስከፈል ሲጀምር፡ የሌለ ክፍያ በጉልበቱ ሲተምን። አይደግፉኝም ብሎ የጠረጠራቸውን አባላት ከኮሚቴ ሲያባርር። በፖሊስ ለማፈን ሲሞክር። ስብሰባ ይጠራና እንወያይ ያሉትን እንደወንጀል በመቁጠር በሃሰት " የከሳሽ ደጋፊ ወይንም ከሳሾች ናችሁ ብሎ የመናገር መብታቸውን በመግፈፉ"............. ነው ብለው ይናገራሉ። ይህንን ደግሞ አልሆነም የሚል እስካሁን አላጋጠመንም። አልሆነም ሲሉ የሰማነው የቦርድ አባላት በፍርድ ቤት በመሀላ ብቻ መሆኑን ታዝበናል። "አባላት አይደሉም ከሚለው ጀምሮ የፈረመ ሁሉ ከሶናል" እስከሚለው ድረስ። ለዚህም ነው ፍርድ ቤት እየተዋሸ ቤተክርስቲያን ተመልሶ ንስሃ ከመግባት ይልቅ ምን ሆንክ? ምን ሆንሽ? ብሎ በመወያየት ዘላቂ መፍትሄ ማግኘቱ ይሻላል የምንለው። ከሳሾች በመክሰሳቸው ሊወገዙ አያስፈልግም መወገዝ ካለብን ተወጋዦቹ እኛ ነን። ችግሩ እየገጠጠ ሲመጣ ስነስርዓት ብለን ቢሆን ኖሮ ዛሬ እዚህ ባልደረሰ ነበርና። ግለሰቦችን አናስቀይምም ብለን አማንያንን እየበታተንን ነው። ባገራችን ሽማግሌ ሽማግሌ የሚባለው በሽበቱ ሳይሆን በበሰለ ተመክሮና አመለካከቱ እንደነበር ማስታወሱ ይጠቅማል። የቤተክርስቲያናችን ችግር ታዲያ የሕግ ብቻ ሳይሆን የሽማግሌዎች መጥፋት ጭምር ነው። የቤተክርስቲያኑን ጉዳይ ከግል የኤኮኖሚ ጥቅም ጋር ካያያዝነው የእምነት መሆኑ ይቀርና የዓለማዊ ድክመት ይሆናል። "ከጎረቤት የነበረው ቤተክርስቲያን ለምን አይገዛም" ብለው የተናደዱት ምእመናን ሳይሆኑ ኮሚሽን የቀረባቸው ደላላዎች እንደነበሩ ትዝ ይለናልና።


አሁንም እንደግማለን ያሸነፈ ሰው የለም የተሸነፍነው ሁላችንም ነን። አንድም ሰው ማጣት ሊያሳስበን ይገባል። ቤተክርስቲያናችን የገንዘብ ችግር አለበት የሚሉን ወደ $48 ሺ ወጪ ሲያደርጉ ግን ቅር አላላቸውም። ከሳሾች ምን ያክል እንዳወጡ በይፋ ባይነግሩንም እንደዚሁ ብዙ ገንዘብ እንደሆነ መገመት ግን ይቻላል።


ለሰላም ጸልዩ






Friday, December 18, 2009

ማንም ሳያሸንፍ ቀረ ቁጥር ፭

በትላንትናው እለት ይጠበቅ የነበረውን የፍርድ ቤት ቀጠሮ ለማየትና ለመስማት ተገኝተን ነበር። ከሳምንት በፊት ዳኛው ለማንም ፈረደ ለማን ተሸናፊና አሸናፊ አይኖርም ብለን መናገራችን ይታወሳል። ትላንት አስችሎ የዋለውን ችሎትም ካየን በኋላ አባባላችን ትክክል መሆኑን ያረጋገጥን ይመስለናል። የከሳሾቹ ጠበቃ " እነዚህ ሰዎች ያላግባብ ዘልፈውናል ቴሬሪስት ናቸው ብለውም ወንጅለውናል" ብሎ መናገር ሲጀምር ዳኛው እሱን መስማት አልፈልግም ብሎ ጠበቃቸውን ሲያስቆመው ስናይ ከተቀመጥንበት ተነስተን እግዚአብሄር ይስጥህ ልንል ምንም አልቀረን ነበር። የቦረዱ ጠበቃ የሃይማኖት ጉዳይ መሆኑን ሊያስረዳ ሲነሳ እሱንም እንዲሁ እሱን ማዳመጥ አልፈልግም ብሎ ሲያስቆመው ስናይና ሁለቱም ወደ ጭብጥ ጉዳዩ እንዲገቡ ሲነግራቸው ሚዛናዊ አመለካከት እንደሚኖር ሙሉ በሙሉ እርግጠኞች ነበርን። የቦርዱን ጠበቃ ለምን ሕጉን ቀየራቸሁ? የቀየራችሁት የማትፈልጉትን አባላት በማባረር፡የምትፈልጉትን ብቻ ይዛችሁ በጥቂት ሰዎች ቤተክርስቱያኑን ለመቆጣጠር መሆኑ ግልጽ ነው። ዛሬ 10 ዓመት ብላችኌል ነገ ደግሞ 28 ዓመት ትሉ ያሆናል ብሎ በንዴት የተናገረው ዳኛ፡ ለመሆኑ ግለሰቦችን ስታባርሩ ወይንም አላስፈላጊ ውሳኔ ስትወስኑ አባላት ምን መከላከያ መንገድ አላቸው? ብሎ የቦርዱን ጠበቃም ጠይቆት ነበር። የቦርዱ ጠበቃ መልሱ የነበረው ያልፈለጉትን የቦርድ አባል በምርጫ ማውረድ ይችላሉ። በተጨማሪም የተወሰነባቸው ውሳኔ አግባብ አለመሆኑን በመጠቆም አቤቱታ ቦርዱ ለሚያቌቁመው የእንባ ጠባቂ ኮሚቴ ማቅረብ ይችላሉ የሚል ነበር። የከሰሰ ከአባልነት ይባረራል አባላትን የሚመርጠው ቦርዱ ነው። ቦርዱ ያወጣውን ከፍያ የማይከፍል ወዲያውኑ መባረር አይደለም እየከፈለም ቦርዱ ካልወደደው አይቀበለውም ያለው የከሳሾች ጠበቃ የተናገረው ዳኛው ለመሆኑ ባዲሱ መተዳደሪያ ደንብ ምን የተቀየረ ሌላ ነገር አለ ብሎ? ለጠየቀው መልሰ ሲሰጥ ነበር። ሕጉን ለመቀየር የቤተክርስቲያኑ መተዳደሪያ ሕግ አንቀጽ 11.1 እና 11.2 ለቦርዱ መብት ይሰጣል አይሰጥም የሚለውን የጠበቆቹን ገለጻ አዳምጦ ውሳኔ እነደሚሰጥ ተናግሮ መልካም ገና ለሁሉም ተመኝቶ ዳኛው ችሎቱን ዘግቶታል።
በግል እንደታዘብነውና ሂደቱን እንደተከታተልነው። ሕጉን ለምን በክስ መሃል ለመቀየር አስፈለገ ለሚለው? የራሳችን መልስ የሚከተለው ይሆናል።
1 የማይፈልጉትን አባላት ለማባረር።
2 አዲስ የሚገቡ አባላትን ለማጣራት ለማበጠር።
3 አባላት ተቀበሉትም አልተቀበሉት የራሳሸውን ውሳኔ በመሰላቸውና ከቦርዱ ጥቅም በመነሳት ለመወሰን።
4 የእምነትን ጉዳይ አስመልክቶ ቄሱ ምን መሰበክ እንዳለበትና እንደሌለበት ለመንገር።
5 አባላት ለመመዝገብ ሲመጡ እንደ አፓርትመንት የማመልከቻ ማስከፈል። አባልነታቸውን ተቀባይነት አገኘም አላገኘ የከፈሉት እንዳይመለስ ማድረግ።
6 ገለልተኛነትን በመስበክ የሲኖዶስን ቦታ መተካት። ነው ብሎ ለማለት ብዙ ጊዜ አልፈጀብንም።
ታዲያ ከላይ ያልነው ተፈጻሚ ከሆነ የተጎዳው ማን ነው? መልሱን ሁላችንም በግል መመለስ ያለብን ይመስለናል። መልሱን ከዳኛ መጠበቅ የለብንም ለማለት ነው። አባላት የሚፈልጉት ይህንን ከሆነ ከሳሾች ቢያሸንፉም መጨረሻው ይኸው ይሆናልና።
ዛሬ ስልጣን ላይ ሆነው ያወጡት ሕግ ነገ ከስልጣን ሲወርዱ መልሶ እነሱንም እንደሚያጠቃ ማወቅ ደግሞ ብልህነትን አይጠይቅም።
ለመብትና ለእምነት ብሎም ለእኩልነት መታገል እንጂ ለማሸነፍና የሌላውን መብት ለመዳመጥ መነሳት መንፈሳዊም፤ ሕጋዊም ፖለቲካዊም መሆን አይችልም።
የዳኛውን ውሳኔ አልሰማንም ምንም ይሁን ግን መፋቀርን አያመጣም። ቤተክርስቲያን የመንፈስ እረፍት ያለበት ቦታ እንጂ የጭቅጭቅ ስፍራ መሆን የለበትምና።
ከፍርድ ቤት ውሳኔ እንሰማለን በውሳኔው ግን አሸናፊና ተሸናፊ አይኖርም።
መልካሙን ለሁላችን እንመኝ።

Sunday, December 13, 2009

ውሸት መጥፎ ነው፡ በተለይ ምንጩ ከቤተክርስቲያን ሲሆን ያስፈራል። ቁጥር ፬

"አንድ አክስቴ የነገረችኝ ትዝ አለኝ" አለን ከመሃከላችን ተቀምጦ የነበረ ጔደኛችን። "ሌባ ገንዘብ ሰረቀና ተያዘ አሉ። እንደተያዘ ወዲያውኑ መስረቁን አመነና የስጋ መቀጫውን ሊቀበል በእስር ቤት እየተዘጋጀ ለነፍሱ ደግሞ ንስሐ አባቱን አስጠርቶ ተናዘዘ። የንስሐ አባቱ ተግሳጽና ምክር ሰጥተው፤ የሚገባውን ቅጣት ከቀጡት በኋላ ልጄ ሁለተኛ እንዳይለመድ፤ ቃል ግባልኝ ብለው ቃል ካስገቡት በኌላ ምክራቸውን ሲለግሱትና ነገሮችን አስፍቶ ማየት እንዲችል ሲያስተምሩት ምን አሉ መሰለህ? ካንተ በላይ እኮ ንስሐ መግባት ያለበት የዘረፍከው ሰውዬ እንደሆነ ታውቃለህ? ምክንያቱም ገንዘቡ እንደጠፋ አላፊ አግዳሚውን፤ ዘመድ ጔደኛውን ተጠራጥሮ ነበርና ብለው አስረዱት" ብላ አጫውታኝ ነበር ብሎ አወጋን። ነገሩ የበደለው ሳይሆን የተበደለም እንዲሁ ሳያውቀው ሃጥያት መስራት ይችላል ለማለት የቀረበ ነው።


በዚህ በከተማችን የተጀመረው የቤተክርስቲያን ሽኩቻ አሁንም እየተፋፋመ፤ እየተጋጋለ ነው። ከሁለቱም ወገን የሚሰነዘሩት አስተያየቶች የሚያስፈሩም የሚያስደነግጡም ናቸው። ከቤተክርስቲያን ይህንን ሰማሁ ካለ አንድ ሰው ማን ነገረህ ብሎ "የወሬ አባቱን" መጠየቅ የተለመደ ሆኗል። ሰብሳቢው ነው ከተባለ አይ ተወው እሱ እኮ በውሸት የተካነ ነው የሱን ወሬ ወሬ ብለህ አደባባይ ይዘህ ትወጣለህ የሚሉ ብዙሃን ናቸው። የሽምግሌዎች (የአማካሪ) ኮሚቴ ለምን ፈረሰ ሲባል ቦርዱን መደገፍ የማይችሉበት ላይ ስለደረሱ ነው ያለን ግለሰብ ለአባባሉ የተለያየ መረጃዎች ሊሰጠን ተነስቶ ነበር። እንዳልሰማን አለፍነው እንጂ።


ሌላው የማስፈራሪያ መሳሪያ ሆኖ የቀረበው ደግሞ የመሃበረ ቅዱሳን ነገር ነው። ለእውነት እንነጋገር ከተባለ ከቤተክርስቲያን አባላት ውስጥ መሀበረ ቅዱሳንን የሚያውቅ ማን ነው? ተብሎ ቢጠየቅ በአዎንታ መላሹ ጥቂት ይሆናል። መሃበረ ቅድሳን የሚለውን ቃል ያስተዋወቀን የቤተክርስቲያኑ ቦርድ እንደነበረ አሌ ማለት የሚቻል አይመስለንም። ጥሩነታቸውን መመስከር ብቻ አይደለም የገንዘብ ድጎ ማ ያደርግላቸው የነበረውም ቦርዱ ነበር። በበጎ አድራጎት ስራዎችም ባገር ቤት አስፈጻሚ እንዲሆኑ የመረጣቸው ቦርዱ ነበር። ዛሬ ተቀልብሶ መሃበረቅዱሳን ማለት በቦርዱ እይታ "ሰይጣን" እንደማለት ሆኗል። ይህ ሁሉ ሲሆን መሃበረቅዱሳን ሲሳደቡም፤ ሲከሱም፤ አላየንም። ትእግስት ያላቸው ግለሰቦች መሆናቸውን ያስመሰከሩ ለመሆናቸው የምንስማማ ይመስለናል።


ባገራችን እንኴን


የምግል ዋሻው ቀሲስ መሸሻ፤
ሲሻው በመስቀል ሲሻው በጋሻ።

ይባል እንደነበር እናስታወሳለንና። ቄስም ሲነደው መቌሚያ ያነሳል ይባል የነበረውን አስታውሰን እነሱ ለፈጣሪ መተዋቸው ይሆን? ብለን በማሰብ በጥንካሪያቸው እንቀናለን። ባንሳሳት ሁለት ዓመት ሞላው መሰለን፤ እዚህ በዳላስ ከተማ መሃበረቅዱሳን አውደ ትርእይት አሳይተውን ነበር። በወቅቱ ለመጀመሪያ ጊዜ መሃበረ ቅዱሳንን እንደ ድርጅት ለማየትም እድል አገኘን። ጥሩ ሥራ ለመስራት በቁጥር መብዛት አያስፈልግ ያልነውም ያኔ ነበር። መሃበረቅዱሳን እምነት፡ ነው፤ መሃበረቅሱሳን ሃይማኖት ነው፤ ለሚሉትና መሃበረቅዱሳን የአባ ጳውሎስ ሰላዮች ናቸው ብለው ስማቸውን የሚያጎድፉትን አይተን፤ ከሀገር ቤት ከቤተክህነት የሚቃጣባቸውን አለንጋ ስናይ ደግሞ ግራ እንጋባለን። አንድ የምናውቀው ግለሰብ መሃበርቅዱሳን ዓርብና እሮብ አትብሉ ይላሉ፤ አለቁርባን ማግባትን አይቀበሉም፤ ከሕግ በላይ ካህንን ያከብራሉ። አገር ቤት የተጎዱ ገዳማትን ሰለረዱ ብቻ የፀደቁ ይመስላቸዋል። በቤተክህነት እውቀታቸው በመመካት የቅዳሴ አይደለም የማህሌት ስህተት አያሳልፉም ብሎ ሲናገር፡ ሌላው ታዲያ ባጭሩ የኦርቶዶክስ ክርስቲያኖች ናቸው አትለንም ብሎ መመለሱ ትዝ ይለናል።

እኛ ውስጣቸውን ስለማናውቅ እንዲህ ናቸው ማለት ይከብደናል። "አክራሪነት መጥፎ ነው" ብለን ሙሉ ለሙሉ ስንቀበል፡ የከረረውን ሳያሳዩን አባባሉን ብቻ የሚነግሩን ከሆነ ማስፈራራት ይሆናል። ቁጭ ብለን ብናወራ እኛም የማንስማማበት ነገር ሊኖር እንደሚችል እንገምታለን። ነገር ግን በጥቅሉ መኮነንን በጅምላ መፈረጁን ነው የምንቃወመው። ባላየነው ወሬ ለመፍራት ደግሞ አረጀን። ለነገሩማ መሃበረ ቅዱሳንን ቦርዱ አስተዋወቀን፤ ዛሬ ደግሞ በመኮነን አይናችሁ ላፈር በሏቸው አለን የሚለውን ለመጠቆም ያክል ነው።

ባለፈው በዚህ ብሎግ ላይ በቤተክርስቲያናችን ክርክር አሸናፊና ተሸናፊ አይኖርም ብለን ለጻፍነው አስተያየት ቀጥተኛ ትርጉም በመስጠት "አዎ ተሸናፊና አሸናፊ ይኖራል" የሚል መልስ በሌላ ብሎግ ማንበባቸን ገርሞናል። ይህ ይጠፋቸዋል የሚሉ ካሉ ተሳሰተዋል። መልስ ላለመስጠት ወሰንንና ብዙዎች አብራሩልን ስላሉ መመለስ የግድ ሆነብን። አሁንም ለማንም ይፈረድ ለማንም ሁላችንም ተሸናፎዎች ነን ብለን እናምናለን። ፍርድ ቤት ይፈርዳል ግን ለማንም ይፍረድ ለማን አንድ እንሆናለን ወይ? ነው ጥያቄው። የተፈረደለት ይፈነጥዝ ይሆናል፤ ሰላም ፍቅር መጣ ማለት ግን አይደለም። ሰላም የሚፈጠረው፤ አንድነት የሚመጣው መነጋገር ሲቻልና ልዩ ነቶችን በጋራ ተወያይተን መፍትሄ ስናገኝላቸው ብቻ ነው።

ሴትዬዋ እርጉዝ ነች እሚለው ላይ ከተስማማን፤ መውለዷ የግድ ነው እዛ ላይ መከራከር አያስፈልግም የሚያዋልዳት ዶክተር የሚረዳት ሆስፒታል እስካለች ጊዜ ብቻ ይሆናል። ወልዳ እንዴት ማሳደግ ትችላለች እሚለው ላይ ግን የዶክተሩ ሚና አይኖርም ለማለት ነው። በዛ ላይ ሚና መጫወት የሚችሉት ቤተሰብና ዘመድ ጔደኛና የሰፈር አዛውንቶች መሆናቸውን መካድ እንዴት ይቻላል? ካልተግባባን ሌላ ችግር አለ ማለት ነው። ስለሆነም በቤተክርስቲያናችን ሰላም መውረድ የሚችለው ሁላችንም ከልህና ከቁጭት ወጥተን በመነጋገርና በመመካከር ብቻ ነው። ወንድሞችና እህቶች ይህ የእምነት ስብስብ መሆኑንም አንዘንጋ።

በመደምደሚያው ባለፈው እሁድ የከርስትና ክፍያ ለአባላት ተነስቷል ተብሎ ሲነገር፤ ለቦርዱ አቤት ብዬ በማሳሰብ ያስፈጸምኩት እኔ ነኝ ያሉን ካህን ከአውደ ምሕረት ቆመው ሲዋሹ አለማፈራቸው እንዳሳፈረን ለመናገር እንወዳለን።

ምሕረቱን ያውርድላቸው።

ሰላም ለሁላችሁ ይሁን

Tuesday, December 8, 2009

ስህተትን ማሰተካከል ሽንፈት አይደለም ቁጥር ፫

ሰላም ለናንተ ይሁን

ባለፈው እሁድ የአስተዳደር ቦርዱ ለከርስትና ይከፈል የነበረውን ክፍያ ማንሳቱን ማስታወቁ ይታወሳል። አጀማመሩ የሚደገፍ ቢሆንም ክፍያው የተነሳው ለቤተክርስቲያኑ አባላት ብቻ መሆኑን ስንሰማ ግማሹ ሊጥ ሆኖ አገኘነው። አባላት ያልሆኑ ክርስትና ለማስነሳት $150 መክፈል አለባቸው የሚለው አሁንም መነሳት ይኖርበታ እንላለን። ወንደሞችና እህቶች፤ ክርስትና በእምነት እንጂ በገንዘብ መገዛት የለበትም። ባለፈው ለምን ማስከፈል አስፈለግ ሲባል "ኢትዮጵያዊ ያልሆኑ ሁሉ እየመጡ በነጻ ስለሚያስነሱ ነው" መባሉ አስገርሞን ነበርና። ከርስቲያን ድንበር የለውም ወንድሞች። ለማንኛውም ይህ እንዲሆን ለታገሉና የተጠየቁትን በስራ ለማዋል ለተነሱ ምስጋናችን የላቀ ነው። በመጭው እሑድ ደግሞ ለማንም ሰው የክርስትና ክፍያ ተነስቷል ብለው እንደሚያውጁ ተስፋ አለን። የአስተዳደር ቦርዱ ቅዳሜ አድርጎት በነበረው ስብሰባ $30 መክፈል የማይችሉ የቤተክርስቲያን አባላት በነፃ አባል የሚሆኑበትን መንገድ ለመወሰን መወያየቱን ስንሰማ ምን አስፈራቸው እንደድሮው ተመልሰናል ቢሉ እኮ ሁሉም ነገር ቀላል ይሆንላቸው ነበር አልን። በተጨማሪም ከ $30 በላይ ይከፍሉ የነበሩ ነገር ግን በአውጅ ክፍያ ጨምረናል ሲባል ተናደው ክፍያቸውን ያቆሙ አንጋፋ የቤተክርስቲያናችን አባላት ወደ ደብራቸው እንዲመለሱ ይረዳል ብለንም እናምናለን።
በሰንበተ እሁድም እንደተለመደው በቤተክርስቲያናችን ያሉ የፖለቲካ ካድሬዎች ከቦርዱ ጋር እንደተነጋገሩ ስነሰማ ምን መአት ሊያመጡ ይሆን ብለን መስጋታችን አልቀረም። እነዚህ ከባሌ ሳይሆን ከጋርላንድ አዝማች ሆነው ጦር ሊመሩ የተነሱ ግለሰቦች በየሳምንቱ የቤተክርስቲያኑን የቢሮ ደረጃ ካልተመላለሱበት እንቅልፍ የሚነሳቸው፤ ከላይ ሆነው ደጀ ሰላሙ ውስጥ ማ ከማ ጋር ተቀምጦ አወራ የሚለው የሚያረካቸው፤ የማይማሩ ወይ የማያስተምሩ ሆነው ስናያቸው ማዘናችንን መናገርም አስፈላጊ ይሆናል። ቦርዱ እነዚህን ግለሰቦች እንደሚያዳምጥ ሌሎችንም ለማዳመጥ ቢችል ኖሮ ምናልባትም እዚህ አለንበት ሁኔታ ላይ አንደርስም ነበር። "በቤተክርስቲያናችን ግለሰቦች እየተሰለሉ ነው" ብለው ሊያሳምኑን የተነሱት እነዚህ ምእመናን ሰላዩ ማን ነው? ሲባሉ "አገርቤት ስልጣን ላይ ያለው መንግሥት"እንደሆነ ይነግሩናል። ወንድሞችና እህቶች በቤተክርስቲያን ውስጥ የሚበጠብጡንን ግለሰቦች ዞራችሁ ተመልከቱና ማንነታቸውን አስተውላችሁ እነሱን ፈርቶ የሚሰልል መንግስት አይደለም ግለስብ ካለ ለጔደኝነት ቀርቶ ለጎረቤትነት አትመኙት። ለመሰለልም እኮ የሚሰለል ሰው መኖር አለበት:: "የሚገርመው የተናጋሪው ሳይሆን ያዳማጩ ነው" ይሉ ነበር በፊት።
በዘር መጡ አልሆነም፤ በፖለቲካ መጡ አልተሳካም፤ ስም በማጥፋት ተሰማሩ አልሰመረም፤ ወረቀት በተኑ አልሰራም፤ ብሎግ ከፈቱ አልተዋጣም፤ የጀመሩት ሁሉ ከሸፈ የሸረቡት ቱሻ ሆነ የተበተቡት ተበጣጠሰ። ካሁን በኋላ ወደ ነበረበት ለመመለስ መንገዱ አንድ ብቻ ነው። ስሕተትን አምኖ ንስሃ መግባት ብቻ። እሱም እምነቱ ካለ።
በነዚህ ግለሰቦች ውሸት የተጭበረበሩት ደግሞ አሁን ነገሩ እየገባቸው እየመጣ ነው። ፈረንጆች "አንዴ አታለኝ ቅሌታም ነህ ሁለት ጊዜ አታለኝ ቅሌታሙ እኔ ነኝ"ይላሉ።
ለቦርድ አባላት ልናሳስብ የምንወደው አሁንም ወደነበረበት ለመመለስ አንዳንድ እርምጃዎች መውሰድ ይኖርባቸዋል።
1. መተዳደሪያ ደንቡን ወደነበረበት መመለስ።
2. የአባልነት ክፍያ ገደብ ማንሳት። የታገዱ አባላትን መመለስ።
3. ቤተክርስቲያኑን የፖለቲካ ሳይሆን የእምነት ቤት ማድረግ።
4. በፖሊስ ሳይሆን በእምነት መመካት::
5. መንፈሳዊ ውሳኔዎችን ለመንፈሳዊ አባቶች መተው።
6. መስራቾችን አባረን ገንዘብ እነዘርፋለን ብለው የተነሱትን በቄስ ማስመስከር መጽሐፈ ቄደር ማስጠመቅ።
አንጋፋ አዛውንቶችን ሰብሰቦ አባላት እንዲወያዩ ማድረግ መፍትሄ ይሆናል ብለን እናምናለን። በተጨማሪ ደግሞ፤ የቤተክርስቲያን ምእመናን በሞላ እውነቱን ለይተን ለእውነት ከቆምን ለመፍተሄው ትልቁን ስራ ሰራን ማለት ይሆናል። የምናምንበትንና እውነቱን እነጂ አዳማጩን እያየን መናገር ካቆምን ወደ ሰላም መመለስ የሚቻል ይመስለናል። ክስ የመሰረቱትም ግለሰቦች ከዚህ የተለየ ፍላጎት ካላቸው ሊነግሩን ይገባል። ብዙ ሰው እንዳለው በዚህ ቤተክርስቲያን ተሸናፊና አሸናፊ መኖር የለበትምና።
ሰላም ዋሉ

Wednesday, December 2, 2009

መሳደብ የመሃይሞች፤ መነጋገር የብልሆች፤መደማመጥ የጠበብቶች ነው። ቁጥር ፪

ቆየት አለ መሰለኝ ዘመኑ። አንድ በጊዜው የትግሉ ሂደት ያልጣማቸው፤ ወጣቶቹ የሚጔዙበት መንገድ ያስፈራቸው፤ የኢድሕ አባል "በሂስና በግለሂስ" ድርጅታቸው ያምን እንደሆነ ተጠይቀው ሲመልሱ " በጭራሽ አናምንም፡ ሂስ ማለት እኮ የጨዋ ልጅን ማዋረድ ማለት ነው። ግለሂስ ደግሞ እራስን ሰድቦ ለሰዳቢ መስጠት ነው። "ብለው ተናገሩ እየተባለ ሲወራ ሰምተን ስቀን ነበር። በወቅቱ የነበረውም መንግሥትም ሆነ ተቃዋሚ ነን ባይ ድርጅቶችም "በሂስና ግለሂስ" እናምናለን ይሉ ስለነበር ነው የሳቅነው እንጂ አባባላቸው ሙሉ ለሙሉ ውሸት ሆኖ አልነበረም። ሂስ ለማረም ከሆነ ትምህርታዊ፤ ለዘለፋ ከሆነ ደግሞ ስድብ ይሆናል። ከግለሂስ መማር ከተቻለ ገንቢ ለፌዝ ከሆነ መሳለቂያ መሆኑ ነው። ዘንድሮ ደግሞ መሰዳደብ ጀግንነት ትእግስተኛ መሆን ደግሞ ፍርሃት ተደርጎ እየተወሰደ ነው።


አንድ ባካባቢያችን የሚጻፍ ብሎግ ለቤተክርስቲያናችን የቦርድ እጩዎች እንጠቁማችሁ በሚል የግለሰቦች ስም ሲጠቁም፡ ተወዳዳሪዎቹ ከታክሲ ነጂዎች ውጭ ተሽከርካሪ ወንበር ላይ የተቀምጡ መሆን አለባቸው ማለቱን ስናነብ ደነገጥን። የዚህ ጽሑፍ ጸሃፊዎችም ሆኑ፡ ሰም ደርድረው ጻፉ ያልናቸው ግለሰቦች በአንድ ወቅት ታክሲ ሲያሽከረክሩ እንደነበር እውቅ ነበርና። ተሽከርካሪ ወንበር የጨመርነው እኛ ነን። ጠቌሚዎቹ ያሉት ግን መሁሮች ይመረጡ ነበር። ታክሲ የሚነዱ የተማሩ ግለሰቦች የሉም ማለታቸው ከሆነ፡ አባባላቸውን መሳብ ሊኖርባቸው ነው።
ክርስቲያን ነህ ወይ? የሚል ጥያቄ የሚጠይቁ፡ መልአክ ለመሆን ሳምንት የቀራቸው የሚመስላቸው፤ የራሳቸውን ስህተት ሳያስተውሉ የሌላውን የዐይን ጉድፍ ሊያጠሩ የሚነሱ፤ ወንድምና እህቶች ያሳዝኑናል። ባንፃሩ "አማኝ ነኝ በኦርቶዶክስ እምነት ይህ ትክክል ነው" ብለው ለማስተማር ስለተነሱ ብቻ እንደወንጀል ተቆጥሮባቸው "አክራሪዎች" አልፈው ተርፈው "ታሊባን" እያሉ የሚጠሯቸውና የሚዘልፏቸው ግለሰቦች እራሳቸውን ዞር ብለው ማየት ይኖርባቸዋል እንላለን። እኛ ለአባላት መብት ለሕግ የበላይነት መታገል አለብን የምንል ሁሉ ሃይማኖትና መብትን በየፊናው መረዳት ካልቻልን የጾምና የፍስክ ወጥ እንደተቀላቀለባት ጿሚ ሆነን እንቀራለን።
ትግላችን ለአስገዶም መብት፡ ወይንም ንግስትን ለቦርድ አባልነት ለማስመረጥ ብቻ ከሆነ ከጅምሩ ችግር አለብን ማለት ነው። ሁላችንም ለሕግ የበላይነት ከተነሳን፡ ደግሞ ዓለም ዘውድ ይመረጥ ዳግማዊ፡ በተናጠል ለውጥ አያማጣም ብለን ማመን አለብን። ዋናው የአባላትን መብት የሚጠብቅ፤ ሕግ እስከነደፍን ድረስና ይህንንም በሥራ እስካዋልነው ድረስ፡ ቀሪውን እንደድሮው እየተረዳዳን ማስተካከል ይቻላል ብለን ማመን ይኖርብናል። እስከዛሬ ቤተክርስቲያችን እዚህ የደረሰው ሊቃውንት የቦርድ አባላት ስለመሩት ነው የምንል ካለን ተሳስተናል። ይልቁንስ ሊቆች መረጥን ብለን እየተመነጠርን ነው። ፈላስፎቹ ዶክተሮችና ነርሶች ለበሽታችን መድሃኒት ሳይሆን መርዝ እያዘዙልን ነውና። ይህንን ጽሑፍ አንብቦ የግለሰብን ሚና ትክዳላችሁ የሚለን ቢኖር ካለሕግና ካለመመሪያ ግለሰብ ብቻውን ምንም ሊያደርግ እንደማይችል ልንጠቁመው እንወዳለን። በነገራችን ላይ ጋንዲም ሞሶሎኒም ግለሰቦች እንደነበሩ አንዘንጋ።


Thursday, November 26, 2009

ይቅርታ የክርስቲያን ባህርይ ነው ቁጥር ፩

በዛሬው (THANKSGIVING) የፈጠረን አምላካችንን ተሰባስበን በምናመሰግንበት እለት፡የሰላም ንፋስ እንዲነፍስ፡ የፍቅር ዝናብ እንዲያካፋ፡ የይቅርታ ጥላ እንዲያጠላብን መፀለይ የተገባ ከመሆንም አልፎ ክርስቲያናዊ ግዳጅችን መሆኑን መቀበል የግድ ይሏል። በቂም በቀል የሚመራ ክርስቲያን ከመሃከላችን ካየን በጸሎት በምክር መርዳትም እንደዚሁ ክርስቲያናዊ ግዳጃችን መሆን ይኖርበታል። እንዳንስማማ የተስማማን ይመስል በሁሉ ነገር ተጣልተን እስከመቼ እንዘልቃለን? ብለንም እራሳችንን ብንጠይቅ ምን አልባት ካንቀላፋንበት እንባንን ይሆናል። ውድ የቤተክርስቲያን አባላት በዛሬው የፈረንጆቹ በዓል እንድታደርጉ የምነጠይቃችሁ ነገር ቢኖር ሁላችሁም በቤተክርስቲያናችን የተከሰተውን መለያየትና መናቆር እንዲቆም በጸሎት እንድታስቡት ብቻ ነው። ከደጋፊና ከተቃዋሚ እየተባለ የሚጻፈውን የስድብ ውርጅብኝ፡ የቃላት ሽኩቻ አንብበናል። "መሳሪያ የታጠቀ ሁሉ ነፃ አውጭ ነው" ማለት ስህተት እንደሆነ ሁሉ፡ የተነገረው በሙሉ እውነት ነው ብሎ መቀበል የዋህነት ይሆናል። እያንዳንዳችን ምን እያደረግን ነው? ብለን እራሳችንን ብንጠይቅ ምንአልባትም የችግሩ መልስ በቀላሉ የሚገኝ ይመስለናል። "ሽማግሌዎች ቢኖሩ ኖሮ እዚህ አንደርስም ነበር" ለሚሉት እውነት አላችሁ እያልን፡ አባባላቸውን ስንጋራ፡ "አሁን ለምን ሽማግሌዎች ሊያስታርቁ ተነሱ" ብሎ መተቸትና መሰናክል ለመፍጠር መነሳት ግን ሌላ ስህተት ነው ብለን ደግሞ እናምናለን። በፍርድ ቤት ትእዛዝ ችግራችን ይፈታል ብሎ የሚያምን ካለ የዋህ ነው ብሎ መናገር ማስፈራት የለበትም። ፍርድ ቤት በሚሰጠው ብያኔ ፍቅር አይመጣም አንድነት አይፈጠርም። ይህ ሊሆን የሚችለው የተለያየ ሃሳብ ይዞ የሚከራከረው ቡድን ተቀምጦ መነጋገር ሲችል ብቻ ነው። ክስ የመሰረቱትን ለምን ክስ መሰረቱ ብሎ መኮነን ደግሞ ሲደረግ የነበረውን መካድ ይህንን ባያደርጉ ኖሮ ዛሬ እንደዚህ ለመናገር የማንችልበት ሁኔታ ላይ እንሆን እንደነበር አለመቀበል ይሆናል። የቤተክርስቲያን ገንዘብ ስላለ ከሳሾቹን ገንዘባቸውን አስጨርሰን እንዲሸነፉ እናደርጋለን የሚሉት የቤተክርስቲያኑ ተመራጮች ማወቅ ያለባቸው ነገር ቢኖር የተመኩበት ገንዘብ ከምእመናን የተዋጣ መሆኑን ነው። ምእመኑ ካልደገፈ የገንዘቡ ቌት እንደሚሟጠጥ ከሳሾችንም ከአሁኑ በበለጠ እየደጎሙ እየደገፉ እንዲቀጥሉ ሊያበረታቱ እንደሚችሉ ማሰብም የተገባ ነው። ከሳሶችም ሆኑ የቤተክርስቲያኑ ተመራጮች ማወቅ ያለባቸው ነገር ቢኖር ያለ ምእመን ድጋፍ የትም ሊሄዱ እንደማይሄችሉ ነው። በተናጠል ቤተክርስቲያን አይገነባምና። ተሰዳደብን፡ ተካሰስን፡ ተወነጃጅለን አሁን ደግሞ ወደ አንድነት ለመምጣት ምን አስተዋጽኦ እናድርግ ብሎ መነሳት ክርስቲያናዊ ነውና ሁላችንም በተናጠል እራሳችንን ጠይቀን ለሰላም እንነሳ። እከሌን ብናገረው እንጣላለን ከመሃበር ያባርሩኛል ያልሆንኩትን ስም ይሰጡኛል፡ ዝምድናችን ይፈርሳል ጔደኝነታችን ይቀራል በቡድን ያጠቁኛል ብሎ በመፍራት ለእውነትና ለመብት አለመነሳት ደግሞ በሕሊና ማስጠየቅ ይኖርበታል እንላለን። ስለሆነም ለሁላችሁም ዛሬ ጥያቄዎች ማቅረብ እንወዳለን። በግል ምን እያደረግን ነው? ሰለኛ ሌሎች እስከመቼ ይወስናሉ? መብትና እምነት፡ ሕግና አምልኮን መለየት የምንችለው መቼ ነው? ከራሳችን ጋር እንዴት እንታረቃለን? መንፈሳዊ አባት እየዘለፍን እንዴት መንፈሳዊ ነን ማለት እንችላለን? መንፈሳዊ አባቶቸስ ከተሰጣቸው ስልጣን ውጪ ሲያልፉ እንዴት እናስቆማቸዋለን? የነዚህን ጥያቄዎች ከመለስን የችግሩን ብዙውን ጎን ቀረፍነው ማለት ነው ብለን እንስማማ።
አሁን ምንእላለሁ ከምንስ ላይ ቆሜ፡
የገደለው ባሌ የሞተው ወንድሜ።ይሉ አልነበር።