Monday, January 25, 2010

ሥልጣን ተዘዋወረ እንጂ ለውጥ አልመጣም። ቁጥር ፱

በትላንትናው ምርጫ የተደሰቱና የተከፉ እንዳሉ እውነት ቢሆንም፤ እኛን ግን አላስደነገጠንም፤ አላስገረመንም። ማንም ይመረጥ ማን በቤተክርስቲያናችን ውስጥ ሰላም ሊመጣ የሚችለው በእምነት ፍቅር ስንቆራኝ በክርስቲያን ወንድምነትና እህትነት ስንጎዳኝ ልዩነታችንን በውይይት መፍታት ስንችል ብቻ ነው ብለን ከማመን ንቅንቅ አላልንም። አሁን እንደሚታየው የተደራጀ የፖለቲካ ቡድን የበላይነቱን ወስዶ ምእመንን አማኝ ሳይሆን ያልተመለመለ ተጋዳይ ስሙን ያልሰጠ የፖለቲካ አባል ማድረግ ይቻላል ከሚል አባባል በመንደርደር ግለሰቦች ቤተክርስቲያኑን ወደ ፖለቲካ መስመር እንወስዳለን ብለው መነሳታቸው የሚያሳዝን ነው። ይህ ደግሞ መሐመድ በግብዣ ላይ አብሮ ስለበላ ብቻ ሳይጠመቅ ክርስቲያን ሆነ እኮ ብሎ እንደማውራት። ገብረየሱስ እነፋጡማ ሰርግ ላይ በመታየቱ ሰለመ ብሎ እንደመመስከር ይሆናል። ይህ ቤተክርስቲያን የአማንያን ሳይሆን የጥቂቶች የተደራጁ ቡድኖች ንብረት ይሆናል የሚል አመለካከት ያላቸው ግለሰቦች እስካሉ ድረስ ሰላም በምንም አይነት ይፈጠራል ብላችሁ እንዳታስቡ። በፊታችን ቅዳሜ ስብሰባ ከሳሽ የተባሉ ግለሰቦችን ከቤተክርስቲያን ለአንዴም ለሁሌም ለማባረር ስብሰባ እንደተጠራ ሰምተናል። ስብሰባ መጠራቱ ሳይሆን ይህ መሆን አለበት ብለው የወሰኑት ዛሬ የመሰናበት እጣ የደረሳቸው የቦርድ አባላት ጭምር መሆናቸውን ሁላችሁም የምታውቁት ይመስለናል። ይህም የሆነው ዛሬ ተመረጡ በተባሉት የቦርድ እጩዎች ግፊት እንደነበረ ሁላችንም የምንስማማበት ጉዳይም ነው። ታዲያ የታለሉት ይህንን ብናደርግ ደግመን እንመረጥ ይሆናል ያሉት እንጂ ይባረሩ የሚባሉት ግለሰቦች አይደሉም። ነገ ከሳሽ ናችሁ ተብለው ሊባረሩ የተወሰነባቸው ግለሰቦችማ ከሁላችንም በፊት ነገሩ ገብቷቸው ልክ ያልሆነን ነገር በመቃወም የመብት መደፈርን ለማስቆም በተቻላቸው ሁሉ ጥረው መፍትሄ ሲያጡ ወደ ሕግ አምርተዋል። ወደ ሕግ ማምራታቸውን ባንቃወምም በፍርድ ቤት ትእዛዝ ደግሞ ፍትህ እንጂ ፍቅር ይመጣል ብለን ስለማናምን አሁንም መፍትሄው መወያየት ነው ብለን ለሁለቱም ወገን መናገር እንወዳለን።


ዘንድሮ እንዴው ነገር እያስፈራን መጣላት እያስጠላን ሌላው አርግዞ እኔ በወልድኩ እያልን መጣንና ዝምታ አጠቃን እንጂ፤ የሚደረገው ነገር ሁሉ ትክክል እንዳልሆነ ሁላችንም በተናጠል የምናወራው ጉዳይ ነው። መረዋ በተደጋጋሚ ይህ ሊሆን እንደሚችል መናገሩም የሚታወስ ነው። አንድ እብድ "ነገ ቤት ይቃጠላል" ስትል አመሸችና የሚያዳምጣት አጣች። ታዲያ በነጋታው የሰውን ቤት ለኩሳ ሲቀጣጠል ሰው ሁሉ ኡ ኡ ማለቱን ሰምታ ምን አለች መሰላችሁ "ነግረናል ቤት ይቃጠላል ብለናል"። እንዴው ወዴት ከፍ ከፍ አትበሉን እንጂ ሌላው ቢቀር በሃይማኖታችን ክርስቶስን ስለገደሉት ክርስትና ተስፋፋ እንጂ አልሞተም ብለን የምናምን ሰዎች እኮ ነን። እስከመባረር የሚያደርስ ቅጣት ሊቀበሉ የደረሱ ምእመናን በመሃከላችን መኖራቸው ደግሞ የሚያኮራን እንጂ የሚያሳዝነን ሊሆን አይገባም።
ባለፈው የቦርድ ስብሰባ ላይ ለጊዜው በሊቀመንበርነት የሚያገለግሉት ግለሰብ ሰባኪ ከውጭ እናስመጣ በሚል ባቀረቡት ሃሳብ የነገው እጩ ሊቀመንበር ለመሆን የቸኮሉት ዶክተር አባ ወልደተንሳይን እናስመጣ በማለት መከራከራቸውን ወይዘሮ ፈትለወርቅም በሃሳቡ መደሰታቸውን እንደገለጹ ስንሰማና ለጉዳዩ ተጋብዘው የነበሩት ካህን መምሬ ሞገስ እንኳን ሳይጠበቅ ግብዣውን ተቃውመው መነሳታቸውን ስንሰማ ወይ ጉድ አላልንም። ለምን ቢባል የዶክተሩ እቅድ ዛሬ ተመረጡ የተባሉትም ተመራጮች እቅድና ትግል የስደቱን ሲኖዶስ ለማስመጣት ነው ብለን ስንናገር ከርመናልና። ሰሚ ያገኘነው ግን አሁን ነው። እንዴውም ከሰሙን አንዱ መምሬ ሞገስ መሆናቸውን ስንረዳ ሃሌ ሉያ የክርስቶስ ተአምር አያልቅም ብለናል።
ውድ የክርስቲያን ቤተሰቦች። ካህናቶቹን ካላባረርን የሚሉት ዶክተሩና አቶ አበራ ዛሬ የተመረጡትን ግለሰቦች ይዘን በድምጽ ብልጫ ምኞታችንን ሥራ ላይ እናውላለን እንደሚሉ ይገባናል። እንደወንድምነታችን ምክር እንለግስ ይህንን ከማድረጋቸው በፊት ቢያስቡበት መልካም ነው።
ለስደት ሲኖዶስ እንሰግዳለን ብለው መነሳታቸውንም ሰምተናል። ስለራሳቸው አያገባንም እኛን ግን ወክለው ይህንን ማድረግ እንደማይችሉ ካሁኑ በግልጽ ልናስቀምጥላቸው እንወዳለን። ተማክረው................... አይሸትም ይላሉና።
አቶ አበበ ጤፉ
ወየዘሮ ሰሎሜም ሆኑ
አቶ ሙሉአለም እንኴን ደስ ያላችሁ የተመኛችሁትን አገኛችሁ እኛ እስከምናውቀው ድረስ ለቤተክርስቲያን አገልገሎት የሚመረጥ ሰው ተጠይቆ እንጂ ተፈነካክቶ መመረጥን ሰምተን አናውቅም። በዚህ መልክ በመመረጣችሁም ተለያይቶ የነበረውን አካል እንዲነጋገር መንገድ በመክፈታችሁ ምስጋና ለናንተ ይሁን። ለመሰንዘር ላሰባችሁት ቡጢም ሆነ እርግጫ ከሚካኤል እርዳታ ጋር ተዘጋጅተን እየጠበቅናችሁ መሆኑንም መንገር ማስፈራራት አይደለም።
ይህንን ቤተክርስቲያን እናፍርስ ብለው የተነሱት ግለሰቦች ህልም እውነት እንዳይሆን የሁሉም ምእመን ግዴታ ነውና ከዝምታ ወጥተን አሁንስ ይብቃ ማለት መቻል አለብን። የተራበ ጅብ ፍየል እያየ በሙዳ ሥጋ አይመለስምና።
ከስልጣን የወረዳችሁት ወንድሞችና እህቶች፡ ሆይ የትላንትናውን ለትላንትና እንተውና ቤተክርስቲያናችንን ወደ ነበረበት ለመመለስ አብረን እንሰለፍ። ግዴላችሁም ስላልተነጋገርን እንጂ ሁላችንም የምንለው " ስልቻ ቀልቀሎ ቀልቀሎ ስልቻ " ሳይሆን የቀረ አልመሰለንም::

Saturday, January 16, 2010

የሰሞኑ ውይይት? ቁጥር ፰

አቶ አያሌው፦ መምሬና ቀሲስ ልዩነቱ ምንድነው?
አቶ ከበደ፦ መምሬ ከቅስና በፊት የሚሰጥ ሹመት ነው።
ዲያቆን ብሩክ፦ ኧረ በወላዲቷ። መምሬም ቀሲስም አንድ ነው። አስተማሪና መምህር እንደማለት መሆኑ ነው ወንድሞቼ አንሳሳት።
አቶ ከበደ፦ታዲያ ቀሲስ መስፍንና መምሬ ዬሃንስ አንድ ናቸው ማለት ነው?
ዲያቆን ሲራክ፦አዎ አንድ ናቸው። ግን ቄስ ሁሉ እኩል እውቀት አለው ማለት አይደለም። ባገራችን "መምሬ እከሌ እኮ ሰሞነኛ ቄስ ነው" ከተባለ ከመቀደስ በስተቀር ምንም እውቀት የሌለው ነው፤ ወይንም መሪ ጌታ አይደለም ማለታቸው ነበር። ታዲያ መምሬው ሆኑ ልጃቸው የሰሞነኛ ቄሶች ናቸው ቢባል እውነት ነው። እንዴውም ወጣቱ ቄስ ቅስናውን ያገኘው ከተወገዘ ጳጳስ ነው በሚል ነፍሳቸውን ይማረውና በወቅቱ ሊቀ መንበር የነበሩት ሻለቃ ክፍሌ "እኔ እያለሁ አንተ በቅስና መቅደስ ውስጥ ገብተህ አትቀድስም" ይሉ እንደነበር ብዙዎች ዛሬም ይናገራሉ። ወደ ጥያቄው እንመለስና መቀደስ የሚችለው ሁሉም ቄስ ሆኖ ሳለ፤ አዲስና ብሉይን አውቆ ማስተማር የሚችለው ግን ጥቂት ይሆናል። ከዚህ አልፎ አቌቌምና ቅኔ፧ ድጔና ፆመ ድጔ ............... እያለ የእውቀቱ መመዘኛ እየሰፋ ይሄዳል። ምን አለፋህ ሁሉም ዶክተር ቀዶ መጠገን አይችልም እንደምንለው አይነት ነው።
አቶ አያሌው፦ታዲያ ለምን ቄስ መስፍን ይባረርልን? መላከ ሳህል ከቤተክርስቲያን ይወገዱልን? ብለው የሚጨቃጨቁት?
አባ መቻል፦ይህ የቀድሞ ፖለቲከኞች ነን ባዮች ጥያቄ ነው። እነዚህ ከኋላ ሆነው ነገር የሚገምዱ ፖለቲከኛ ነበርን ባዮች ሰላም ከተፈጠረ ታመው የሚያድሩ አይነት ናቸው። በቀድሞው የደርግ ትግል ዘመን በሰሜን አሜሪካ የተማሪዎች ማህበር ውስጥ ሆኜ በቦስተን ስታገል ነበር የሚሉትን ግለሰብ ያጠቃልላል። መዋሸት ደግሞ የከረመባቸው ናቸውና ተዋቸው እየተባሉ የሰነበቱ ናቸው። እሩቅ ሳትሄድ እዚሁ ሚካኤል ቤተክርስቲያን አካባቢ ያሉ የቀድሞ የሰሜን አሜሪካ ተማሪዎች ማህበር ESUNA አባላት የነበሩ ግለሰቦችን ብትጠይቃቸው ግለሰቡ በተማሪዎች ትግል ውስጥ እንዳላለፉ ይነግሩሃል። የቦስተኑ ታሪክ ሌላ ነው። ካስፈለገ በሰፊው መተረክ ይቻላል። ታዲያ በሕይወታቸው ጥሩ እንደመስራት እራሳቸው የቦርድ ተመራጭ ሆነው "እውቀት አለኝ የትግል ተመክሮ አለኝ" የሚሉትን በሥራ እንደመተግበር ቤተክርስቲያንን ለምን እንደሚያምሱ መመለስ ያለባቸው እራሳቸው ይሆናሉ። ችግሩ ደግሞ በተፈጥሮ የበታች ብቻ እንጂ የእውቀት የበላይ እንዲኖር የማይፈልጉ ግለሰብ በመሆናቸውም ሊሆን ይችላል። ግለሰቡ ሊቀ መንበሩን እየወተወቱ የሰነበቱትን ቄስ እየጠመዘዙ፡ ለመጥፎ መሰለፍን እንደምርቃት የተቀበሉ በህይወታቸው ምንም ሳይሰሩ በመቆየታቸው ሌላው በሚሰራው በቅናት የሚቃጠሉ ግለሰብ ናቸው ብዬ አምናለሁ።
አቶ አያሌው፦ እውነት ቄሶቹን ያባርራሉ ብላችሁ ታምናላችሁ?
አባ መቻል፦ይህ እራሱን የቻለ የፖለቲካ ጥያቄ ነው። ነገሩን በመለወጥ ቀሲስ መስፍንን በጀት የለንም ብለው ለመቀነስ እንዳሰቡ የተረጋገጠ መረጃ አለ። መላከ ሳህልን ለጊዜው አባላትን ለማረጋጋት እናቆያቸው እያሉ መሆኑንንም ሰምተናል። ቀሪ ሁለት ቄሶችን አስመልክቶ ግን መግባባት አለ። በመጀመሪያ ከቴክሳስ የመንግስት ድጎማ ካህኑ አባት እንዲያገኙ ደሞዛቸው ለሁለት ተከፍሎ ለካህን ልጃቸው እንዲሰጥ ተደርጎ ያሉ በመሆኑ የመንግስት ድርጅቶችን ለማታለል በተደረገው መረብ ውስጥ ያለ ጉዳይ በመሆኑ ቤተክርሰቲያኑን ሊያስጠይቀው ስለሚችል ያልተቀጠረው ወጣት ካህን እንደተቀጠረ ተቆጥሮ መሰንበቱ የማይቀር ነው።
አቶ አያሌው፦ቄሱ መንግስትን እያታለሉ ነው ለዚህም ቤተክርስቲያናችን ለወንጀሉ ተባባሪ ነው የምትለን?
አባ መቻል፦ አዎ ይህንን የማያውቅ ሰው አለ ብለህ ነው? ሁሉም ያውቃል ግን ለመናገር ፍራቻ አለበት።
አቶ ከበደ፦ አዲሱን የቦርድ ምርጫ እንዴት ታየዋለህ?
አባ መቻል፦ ምን እሚታይ አለበት የፖለቲካ ስብስብ እየሆነ ነው። አቶ አበበ የአገራችን ድንበር ተወሰዶ ለሱዳን ተሰጥቷልና እናስቁም የሚለው ኮሚቴ አባል ነኝ ባይና በፖለቲካ ፓልቶኮች የኢኮኖሚ ጠበብት ተብለው ይናገሩ የነበሩ ግለሰብ ዛሬ የቤተክርስቲያን ተመራጭ እጩ ሆነው መቅረባቸውን ያሰተዋለ ግለሰብ ያለውን ላካፍልህ " እንጀራ ስለሸጠ የኢኮኖሚ ጠበብት ነኝ ብሎ ባደባባይ ፓልቶክ ላይ የቀረበ ፖለቲከኛ ግለሰብ ዛሬ ካህን ነኝ ቢልስ ምን ይገርማል" ብሎ ነበር የደመደመው። ሌሎቹ የየራሳቸው ምክንያት አላቸው። ልጃቸውን ወደ ፕሮቴስታንት ቤተክርስቲያን እየላኩ የኛን ልጆች እገስጣለሁ የሚሉት ወይዘሮ ሰሎሜ ጭምር ጥረታቸው እየተሳካ እየመጣ መሆኑን ታያለህ። ስልጣናቸውን በቅርቡ የሚነጠቁት ሊቀመንበር ኮሎኔል አጥናፉን ይመስሉኛል። የመንግስቱ ኃይለማርያምን የአሰራር ጥበብ የተካኑት ደግሞ የቦርዱ ዶክተር ናቸው።
አቶ አያሌው፦ አሁን ገባኝ አቶ አበራ ሃምሳ አለቃ ለገሰ መሆኑ ነው። ሌላ ያልተነሳ ነገር አለ? ሲኖዶስና የስደት ሲኖዶስ ምንድነው? ለግንዛቤ ያክል ባውቀውም እንደገና አስረዳኝ።
ዲያቆን ሲራክ፦ጥያቄው ለኔ ይመስላል? ሲኖዶስ የኦርቶዶክስ እምነታችን የበላይ አካል ማለት ነው። ሲኖዶስ እንደ ፖለቲከኞች የፓርቲ አወቃቀር ብንወስደው የማእከላዊ ኮሚቴ አይነት ማለት ነው። በውስጡ ጳጳሳት ያሉበት የሃይማኖታችን የበላይ ኮሚቴ ይሆንና ኮሚቴው ከመሃከሉ ሊቀመንበር ይመርጣል ተመራጩ ፓትርያርክ ሆኖ ይሰየማል ማለት ነው። ታዲያ የቀድሞው ፓትርያርክ "ታምሜያለሁና በቃኝ" ብለው ካገር ስለወጡ አባ ጳውሎስ በምርጫ ፓትርያርክ ሆነው ተሰየሙ። በነገራችን ላይ የቀድሞው ፓትርያርክ አሜሪካ በስደት ከመጡ በኋላ በስደት ቤታቸው የድሮውን ስምና ስልጣን በመፈለግ የስደት ሲኖዶስ ይቌቌም ብለው በሰሜን አሜሪካ ሌላ ሲኖዶስ እንዲቌቌም አደረጉ ማለት ነው።
ወይዘሮ ሰላማዊት፦አባ ጳውሎስ ዘረኛ ናቸው እየተባለ ትግሬነታቸው እየጎላ ከኢህአደግ ጋር ያላቸው እስስርና መመሳጠር እየተነገረ መንግስት እንደሾማቸው ለምን ይወራል ታዲያ?
ዲያቆን ሲራክ፦ ካቅሜ በላይ የከበደ ጥያቄ እየጠየቃችሁ እኔንም ኃጥያት ልታናግሩኝ ነው። የሆነ ሆኖ፤ በአገራችን ታሪክ ጳጳስ መሰየም የተጀመረው (ኢትዮጵያዊ ጳጳስ ለማለት ነው) በአፄ ኃይለስላሴ ዘመነ መንግስት ነበር። ከዚያ በፊት ጳጳሳት የሚላክልን ከግብጽ ከአለክሳንድርያ እንደነበረ የሚታወስ ነው። ጃንሆይ ያቌቌሙት ሲኖዶስ የእሳቸውን ስልጣን እሚቃረን ጳጳስ ስልጣን ላይ አላወጣም። ደርግ ስልጣን ላይ ሲወጣም ጭቁን መነኩሴ ፈልጉልኝ ብሎ ሕዝባዊ ለማድረግ፡ በባዶ እግራቸው የሚሄዱ መነኩሴ አስፈልጎ ማስመረጡ እሙን ነው። ደርግ ይህንን ሲያደግ ለኦርቶዶክስ አስቦ ወይንም ሃይማኖት ኖሮት አልነበረም። በመካከሉም የጎንደር የኢሰፓ አንደኛ ፀሐፊ በነበረው በገዛኸኝ ወርቄ አቅራቢነት አቡነ መርቆሪዎስ የጎንደር ክፍለሃገር ጳጳስ ስለነበሩና "ሞቴም ሽረቴም ከዚህ መንግሥት ጋር ነው" በማለታቸው ከመንግስቱ ኃይለማርያም ፊት ቀርበው ቃል ገብተው ለመመረጣቸው የዐይንና የጆሮ ምስክሮች እዚህም ዳላስ ይገኛሉ። ከዚህ በመነሳት መንግሥት የሚደግፊውን ጳጳስ አያስመርጥም የሚል ይገኛል ብዬ አላምንም። ለነገሩማ በነፍስ ግድያ የተካነው ሻለቃ መላኩ ተፈራ የደብረታቦር ልጅ መሆኑን አትዘንጋ ያውም የፋርጣ ተወላጅ። ታዲያ የስደት ሲኖዶስ የሚሉት ጳጳሳትም ሆኑ እዚህ የሚያምሱን አሁን ለቦርድ እጩነት የቀረቡትም አቶ ሙሉአለም ጭምር እንዲሁ የፋርጣ ተወላጅ መሆናቸውን ታውቅ ነበር? የመላኩ ዘመድም እንደሆኑ ይነገራል። ሻለቃው ጅቡቲ ሸሽተው ወጥተው በነበረበት ሰዓት ወደ አሜሪካ ለማሰወጣት እዚህ የተደረገውን ጥረትም ሰዎች እስካሁን ያወጉታል። ደግነቱ ኢህአደግ ጠልፎ በወህኒ ከተታቸው። ዛሬ የሞት ፍርድ ከተፈረደባቸው የቀይ ሽብር ወንጀለኞች አንዱ እኝሁ ሻለቃ ናቸው። ይህን የማነሳልህ በአገር ልጅነት ሁሉንም ለመወንጀል ሳይሆን ግንኝነቱን ተከታትለህ እንድታውቅ ለማድረግ ነው። የስደት ሲኖዶሱ የፋርጤ ስብስብ ለመሆኑ ስለማይካድም ነው። አንተ በዘር እየተደራጀህና እየተሰባሰብክ እንዴት ሌላውን ትወነጅላለህ ብሎ ለማለትም ያክል ነው።
አቶ ከበደ፦ዲያቆን የሚለው እውነት ነው። ነገር ግን ፍትሓነገሥቱ ፓትርያርክ በሕይወት እያለ ሌላ ፓትርያርክ አይሾምም ይላልና ነው የስደቱ ሲኖዶስ አሁንም ስልጣኑ የእኔ ነው የሚለው። ይህንን እነዲያቆን አይነግሩህም። ለምን መሃበረ ቅዱሳንን በመደገፉ። መሃበረ ቅዱሳን ደግሞ በአባ ጳውሎስ የተቌቌመ የጠረባ ቡድን ነው።
ዲያቆን ሲራክ፦ እግዚአብሔር ይቅር ይበልህ። የተናገርከው የእውነትም የሃሰት ድብልቅ ነው። እርግጥ ነው ፍትሐነገስቱ ጳጳስ በሕይወት እያለ ሌላ ጳጳስ አይሾምም ይላል።ንጉሥ እያለ ሌላ ንጉሥ አይነግስም እንደሚለው ሁሉ። ደርግ ስልጣን የያዘው ንጉሱ ሞተው አይደለም። ደርግ የመጀመሪያውን ጳጳስ ሲሾም በወቅቱ የነበሩት ጳጳስ አቡነ ቴዎፍሎስ በእስር ቤት እነደነበሩ አትዘንጋ። ፍትሐ ነገሥቱ አንድም ቦታ ሞት የፈራ መነኩሴ ይሰደድ አይልም። መነኮሰ ማለት እኮ ሞተ ማለት ነው። ታዲያ የሞተ መነኩሴ እንዴት ይሰደዳል። አመመኝ አልቻልኩም ካለ ግን መብቱ ይመስለኛል። ያላመመውን ታምሜአለሁ ካለ ደግሞ ዋሸ ማለት ነው። ታዲያ መነኩሴ ይዋሻል? ለውይይትም አይመች ነገር። መሃበረ ቅዱሳንን አስምልክቶ የተናገርከው ግን ይቅርታ አድርግልኝ ውሸት ነው። መሃበረ ቅዱሳንን ያቌቌሙት አባ ጳውሎስ ሳይሆኑ ብጹእ አባታችን አቡነ ጎርጎሪዎስ የሸዋ ክፍለ ሃገር ስብከት ሊቀ ጳጳስ ሲሆኑ ስሙን የሰጡአቸው ደግሞ አቡነ ገብርኤል እንደነበሩ ይነገራል። መሃበሩ የጠረባ ቡድን ሳይሆን ለሃይማኖት መስፋፋት ለኦርቶዶክስ እምነት መጠናከር የተቌቌመ ድርጅት መሆኑን ብትናገር የሚሰራውን ስራዎች አመስግነህ ድክመቱን ብትጠቁም ልቀብልህ እንችል ነበር። የሚሰራ ይሳሳታልና። ያልሆነ ስም መስጠቱ ግን አንተንም ትዝብት ላይ ይጥልሃል። መሃበሩ አባቶችን እንደአባትነት ተቀብሎ ስህተቶች መታረም አለባቸው በማለት በውስጥም የሚታገል ድርጅት ነው።
ወይዘሮ ሰላማዊት፦ዲያቆን ከጀመርን እንጨርሰው የቤተክርስቲያናችን እጣ ምን ይመስልሃል?
ዲያቆን፦ እሱን ለፖለቲከኞቹ ልተውላቸው። የእምነት ሳይሆን ችግሩ የፖለቲካ ነውና።

Friday, January 8, 2010

የተቀበረ ነቀርሳ ቀኑን ቆጥሮ ይነሳ ቁጥር ፯

የፈረንጁ ብቻ አይደለም የአበሻውም ገና ማለፉ እሙን ነው። ያላለፈውና ገና እያናወጠን ያለው የቤተክርስቲያናችን ችግር ግን እያገረሸበት ለመሆኑ ምስክሮቹ የቦርድ አባላት ይሆናሉ ብለን እናምናለን። እንደተለመደው ክሱ ቀጥሏል ብለው በፊታችን እሑድ እንደሚናገሩ መጠርጠራችን አልቀረም። እነሱ ከመናገራቸው በፊት መናገር ደግሞ ትንቢተኛነት ስለሚያስመስል ከመናገር እንቆጠባለን። ለመንደርደሪያ ግን ቦርዱ ከሳሾችን ከቤተክርስቲያን ላንዴም ለሁሌም ማባረር አለብን ብለው እየተወያዩ ለመሆኑ ግን ተጨባጭ መረጃ እየደረሰን መሆኑን ሳንነግራችሁ ብናልፍ በሌሎች የምንጠላውን ውሸት መለማመድ ይሆናል ብለን እንፈራለን። ሰዎችን በማቅረብ እንጂ በማባረር ሰላም ይመጣል ብለን እንደማናምን መናገር ደግሞ ክርስቲያናዊ ብሎም መብታዊ ግዴታ ነው ብለንም እንቀበላለን። ወንድሞችና እህቶች። ቦርዱ ሕጉን ለመቀየር የተነሳሳው " የተጀመረውን ክስ ለማክሸፍ በማሰብ ብቻ ነው" ብለው ድጋፍ ሰጥተናል የሚሉት ምእመናን ማወቅ ያለባቸው ጉዳይ ቢኖር ቤተክርስቲያን የእምነት እንጂ የፖለቲካ መድረክ አለመሆኑን ነው። ለእውነት ቆሞ መታገል እንጂ በውሸት ማመን እንዴት ክርስቲያናዊ ወይም ሃቅ ሊባል ይቻላል? መነሻው ምንም ይሁን ምን ወሸት ውሸት ነው። ፈረንጆች እንደ ዳክዬ ከጮኸ እንደ ዳክዬ ከተንቀሳቀሰ፡ እንደ ዳክዬ ላባውን ካራገፈ፡ አትጠራጠር ዳክዬ ነው ይላሉ። ለእውነት ያልቆመ ካህን ስለ እውነት ማስተማር እንደሚከብደው ሁሉ የማያምን ሰው ስለ እምነት መመስከር ቢከብደው መገረም የለብንም። መረዋ በመደጋገም በዚህ የቤተክርስቲያን ክርክር ሁላችንም ተሸናፊዎች እንጂ አሸናፊዎች አንሆንም ብለን በመደጋገም መናገራችን ይታወሳል። ይህንን አቌም የያዝነው በፍርሃት ሳይሆን የታየን እውነታ ስለሆነ ብቻ ነው። አሁንም ከዚህ ንቅንቅ አንልም። የአስመራጭ ኮሚቴው የሚጠቆሙ አባላት አጥቶ መቸገሩን እያየን በሁለት አባላት ምርጫ ብቻ አንድን ግለሰብ የቦርድ አባል እናደርጋለን ብሎ መነሳት ለዳላስ ምእመናን ስድብ ካልሆነ ምን ሊሆን እንደሚችል መገመት ተቸግረናል። ስለሆነም መረዋ ከተላንቱ በተለየ መንገድ አቌም ለመውሰድ እየተገደደ ነው። ቦርዱና የቦርዱን ስራ አወዳሾች በሰከነ መንፈስ እንደገና እራሳቸውን መገምገም አለባቸው እንላለን። በቆየ የፖለቲካ ምስክርነት እንኴን የመኤሶን ከደርግ መሰለፍ በወቅቱ ጠቅሞ ሊሆን ይችላል፡ በመጨረሻ ሰለባ ከመሆን እንዳልዳነ ግን ያየነው ሃቅ ነው። የሕጉን አንቀጽ 11.2 ሳንቀይር የቦርዱን ወንበር አንለቅም ያሉት የቦርድ አባላት እኛ ከወረድን በኋላ ቦርዱ ሌላ ሕግ እንዳያወጣ ለመቆጣጠር እንዲያስችለን ነው ማለታቸውን ስንሰማ አልሳቅንም አዘንን እንጂ። ትክክል እንዳልነበሩ ልቦናቸው ያውቀው እንደነበረ እየመሰከሩ በመሆኑ። ለዚህም ነበር መረዋ ዛሬ የሚወጣው ሕግ ነገ ከስልጣን ሲወረድ እነሱኑ ሊያጠቃ እንደሚችል ቀደም ብለን የተናገርነው። እናቶችና አባቶች ለካ እውነት ትንቢተኛ ያደርጋል። "ዘረኛ ሆነው ሌላውን ዘረኛ የሚሉ ደካሞች ናቸው" ያለን አንድ ግለሰብ ለምን እንዲህ እንዳለ ስንጠይቀው "ዘረኝነት ከመሃይምነት የሚመጣ ብቻ ሳይሆን የደካማ ሃሳብና እምነት መጠለያ ዳስ ነው በሚል ነው" ብሎን አረፈ። ይህንን ቤተክርስቲያን ለማዳን ወደነበረበት ለመመለስ የሚታየን አማራጭ አንድ ብቻ ነው። ይኸውም ችግራችን ምንድነው? ብሎ ከማንኛውም ያገባኛል ከሚል ግለሰብ ጋር በመወያየት ብቻ ነው። በውይይት አይፈታም የሚሉ በኛ እምነት አንድም እውነት የሚያስፈራቸው፤ ካልሆነም በምእመናን እምነት የሌላቸው፤ ካልሆነም የሚደብቁት ያላቸውና፤ ለወደፊቱ የተንኮል ይፋ ያልሆነ እቅድ ያላቸው ብቻ ናቸው። ቤተክርስቲያኑን ለአባ ጳውሎስ አሳልፈው ሊሰጡ ነው የሚሉት ግለሰቦች በተዘዋዋሪ ምእመናን ምንም የማያውቁ የሚነዱ ግለሰቦች ናቸው ብለው እየተሳደቡ መሆኑን ይዘነጋሉ። ምእመን ካልፈቀደ ምንም ማድረግ እንደማይቻል ካመንን የሚያስፈራ ምንም ነገር አይኖርም ማለት ነው። ወደ 1000 ተጠግቶ የነበረው የቤተክርስቲያን አባል ከመቶ በታች ሲወርድ ካላስፈራ ያላስፈራቸው ሰዎች እቅድ ምን ይሆን? ብሎ መጠየቅ ተገቢ ይመስለናል። ክፍያ ያቃታቸውን አባላት የሚያጠና ኮሚቴ ከማቌቌም ይልቅ አባላት እንደፈቃዳቸውና እንደችሎታቸው ይክፈሉ ማለት የተሻለ ለመሆኑ ተከራካሪው ማን ይሆን? የተቌቌመው ኮሚቴ መመዘኛው ምን ይሆን? የታክስ ወረቀት ወይንስ የግለሰቡ የመሃላ ቃል? የምችለውን ልክፈል ያለውን የለም ትዋሻለህ እያልነው አሁን እንዴት ሊታመን ይችላል? የመንግስት ድጎማ የሚያገኝ ከተበለ ደግሞ በተዘዋዋሪ ድጎማ የማያገኘው ቁጥር ስንት ይሆን? የትኛው ኢትዮጵያዊ ነው ቤተክርስቲያን መጥቶ ችግረኛ ነኝ እርዱኝ የሚል? አባል ባይሆን ምን ሊቀርበት? ለመሆኑ የቦርድ አባላት ይከፍሉ የነበረው የወር መዋጮ ስንት ነበር? አዲስ የቦርድ ምልምሎችስ? መናገር ያለብን አልመሰለንም እንጂ መዘርዘሩ ቀላል ነው። 100 አባላት በ$30 ማሰባሰብ ይሻላል 1000 አባላት $10? ምነው የሂሳብም ችግር ያለ ይመስል?

ወንድሞች እህቶች፤ አባቶች እናቶች ከየትም ወገን ይምጡ ከየት አታውቁም የሚሏችሁን አትቀበሉ። አይገባችሁም ለሚሉ አትስገዱ። በይሉኝታ አትታሰሩ፤ ሌባውን ሌባ ከሃዲውን ከሃዲ ማለት ከጀመርን ምን አልባት አወቁብን ማለት ይጀመር ይሆናል። በመለማመጥ ለውጥ አይመጣም። እኛ ካልተመረጥን ካህናቶቹን ያባርሯቸዋል የሚሉን የቦርድ አባላት እዚህ እንድንደርስ ያደረሱን እነሱ ጭምር መሆናቸውን እንዴት አሌ ሊሉ ይችላሉ? ከተመረጡ ያፈርሱናል የሚሏቸውስ ግለሰቦች እንዲሰባሰቡ ያደረጔቸው በየግብዣው ሲያዞሯቸው የነበሩት እነሱ አልነበሩምን? እስቲ ሁላችሁም እራሳችሁን ጠይቁ። አሁንም መፍትሄ ብለን የምናምነው በችግሮቻቸን ዙሪያ መነጋገር ስንችል ብቻ ነው። አሁንም አሸናፊ አይኖርም:: አሸናፊዎች እኛን አለያይተው የቤተክርስቲያኑ አባላት እየቀነሰ ስለሆነ ቤተክርስቲያኑ ይሸጥና መለስተኛ ቤተክርስቲያን እንግዛ በማለት ገንዘቡን በደላላነት በውሸት ደረሰኝ እንወስዳለን ካልሆነም የስደት ሲኖዶስን በበላይነት አምጥተን ተሸፋፍነን እናመልጣለን የሚል እቅድ ያላቸው ብቻ ይሆናሉ።