Saturday, March 9, 2013

ጉቦ የተቀበለ ዳኛ የሚፈርደውን መረጃውን ሳያገናዝብ አስቀድሞ ያውቀዋል።

"ዝምታ  ወርቅ ነው" "ዝም ባለ አፍ ዝምብ አይገባበትም" ሲባል እንሰማና "ካለመናገር ደጃዝማችነት ይቀራል" "በሽታውን ያልተናገረ መድኃኒት አይገኝለትም" የሚለውን አባባል ስናዳምጥ ደግሞ ግራ እንጋባ ነበር። አሁን ግን ተረት አይደለም ምንም ነገር አያታልለንም። በመቆየት አረጀንና ከእድሜ ጋር ትእግስትም መጣ ቢባል እውነት መሆኑ እኮ ነው። አይገርምም? አገር ቤት ቢሆን ኖሮ አባባ፣ እማማ፣ ተብለን ወንበር የሚለቀቅልን፣ ስንገባ ነወር የሚባልልን፣ ሽማግሌዎች፣ ላስታራቂነት የምንፈለግ፣ የሰፈር ሕጻናት የሚፈሩን፣ የሚያከብሩን፣ አዛውንቶች እንሆን የነበርን ዛሬ እዚህ ባለንበት ሃገር፡ በስድብ ይወርዱብናል፣ የምናየው ደስ አይልም። ለምስክርነት የተቃወሟቸውን ግለሰቦች በሞት የተለዩ ወንድማቸውን እንኳን ባደባባይ እንዳይሰናበቱ፣ እንዳያለቅሱ ሲከለክሉ አስተውለናል። ሊደባደቡም ይቃጣቸዋል፣ ያስፈራራሉ። በደፈናው እዚህ ዳላስ ያልደረሰ ውርጅብኝ ምን አለ? ያም ሆኖ ግን ይህንን መላና  ዘይቤ  ብለው የተነሱ እየተጋለጡ መጡ እንጂ፣ የሚናገሩት እስኪጠፋቸው ድረስ ያልሆነ ያልተደረገ አወሩ እንጂ፣ በቤተክርስቲያን ሽፋን የፖለቲካ አጀንዳ ይዘው በፖለቲካ የራቃቸውን በእምነት ሽፋን ገቡበት እንጂ፣ አባላቱን በተኑት እንጂ፣ ምንም ያተረፉት ነገር እንደሌለ ምስክሩ ምእመኑ ነው። የምናወራው ስለ ዳላስ ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን የችግር ጉዞ  ነው።

የቤተክርስቲያኑ ተመራጮች፣ ካህናትን አባረሩ፣ የሚሰበከውን እኛ አስቀድመን ማወቅ አለብን አሉ፣ ችግራቸው ግን  አልተፈታም።
እንዴት ቤተክርስቲያን ይከሰሳል እኛ እንደልባችን ፈልጠን ቆርጠን እንግዛችሁ አሉ። ሕዝቡ ግን መክሰስ የሚያውቅ ሰው እኮ የሕግን የበላይነት የተቀበለ ነው አላቸው። አትናገሩ ብላችሁ ስታፍኗቸው፣ በፖሊስ መቅደሱን ስታስደፍሩ፣ ምን ማድረግ ነበረባቸው? ብሎም ጠየቃቸው። መልስ አልነበራቸውም። ያም ሆኖ  ሕዝቡ ግን ምን መአት ወረደብን ብሎ ወደ  ፈጣሪው እግዚኦ ማለቱን አላቆመም። በወንጀል ባደባባይ እየተከሰሱ እንኳን አበስ ገበርኩ ሳይሉ አሁንም የመንፈሳዊ ቤት መሪዎች  ነን ሲሉ ቅር አላላቸውም። ስለ ልጆቻቸው ሳይናገሩ ስለ ልጆቻችን ሊነግሩን ይፈልጋሉ። ስለ ባለቤቶቻቸው ሳያወሩ ባለቤቶቻችንን ሊወርፉ ይነሳሉ። የብዙውን ግለሰብ ሥም በየብሎጉ በውሸት እያብጠለጠሉ፣ ትዳር ሊያፋቱ፣ ጎጆ ሊያፈርሱ፣ ተነስተው ያሰቡት ሳይሆን ቀርቶ የተገላቢጦሽ ችግሩ በራሳቸው ላይ ሲመጣ እንደ ምልክት ቆጥረው አምላክን ሲማለዱ ግን አላስተዋልንም።

አንድ ነገር ግን እውነት እየሆነ  መጣ። በሕግ አምላክ ያሉት ግለሰቦች የተናገሩት አንዱም ከመሬት ጠብ አላለም። የዛሬ 4 ዓመት የጻፉት በቅደም ተከተል እየደረሰ  ነው። አሁንም እኛ ያስተዋልነውን እንንገራችሁ። የምናስበውን ካላደረግን ከሥልጣን አንወርድም የሚሉት ባለስልጣናት ይህን ማድረጋቸው መብታቸው ነው ለማለት ግን ጊዜ  አይወስድብንም። ሕጉን እንደፈለጋቸው መቀየር ይችላሉና። የዛሬ  ሳምንት ባዋጅ  ያራዘሙትን የምርጫ ጊዜ እስከ ማርች አይደለም እስከ ኦሜጋ ማድረግ ይቻላቸዋል። መንግሥት እነሱ ናቸውና። ማርች ያሉት ደግሞ ጾም ይገባልና  በጾም መሰብሰብ አይቻልም ብሎ ቀኑን ለማራዘም እንደሆነ  የሚጠፋው ሰው ይኖራል ብለው ያስቡ ይሆን? እንደዚህ ካሰቡ ተሳስተዋል። ትላንት ሲያደርጉት በማየታቸን ለኛ አዲስ አይደለምና?። የአባልነት ክፍያ ከስድስት ወር በላይ ያዘገዩትን በመሃል ተናደውባቸው የነበሩትን ጓዶቻቸውን ለመመለሰ የመክፈያውን ጊዜ አንድ ዓመት እንዳደረጉት ሁሉ ሌላም የመቀልበሻ  አዋጅ ማወጅ ይችላሉ። ሕግ እነሱ ናቸውና። የሚነዳቸው ነገር ቢኖር የመንግስተሰማያት ቁልፍ በእጃቸው አለመኖሩ ብቻ  ይመስለናል። ያ ስልጣን  እነሱ ጋ ባለመኖሩ  ፈጣሪ ምስጋና ይግባው እንላለን።  ከዛሬ  ጀምሮ  የቦርድ አባል መሆን የሚችለው ከደብረታቦር  አውራጃ ከፋርጣ ወረዳ  የመጣ ብቻ  ነው ማለት ይችላሉ። ትግሬ  ከሆንክ የሸዋ ሰው የደቡብ ከሆንክ እኛ የምንለውን የምትቀበል ከሆነ  መልካም ካልሆነ ግቢያችንን ልቀቅ ማለት መብታቸው ነው። ሕግ በእጃቸው ነውና።  የምእመናን ግዴታ ደግሞ እነሱ ያሉትን መቀበል ብቻ ነው። እምቢ አሻፈረኝ የሚል ካለ ከቤተክርስቲያኑ ይባረራል፣ ተባሯልም። ይህ አልሆነም? አይደረግም? የሚል ካለ ለቤተክርስቲያኑ የለፉ እምነት ያላቸው ፈሪሃ  እግዚአብሔር ያደረባቸው ምእመናን ሰላም ባሉ ፍቅር በመናገራቸው የእምነትና የትግል የመደብ ጀርባቸው ተመርምሮ ከአባልነት የተከለከሉ የመስራች አባላት ስም መደርደር ይቻላል። የሚያሳፍረው ግን የሚያባርሩትንና የተባረሩትን ማመዛዘን  ሲጀመር ነው።

የቀድሞ  የቦርድ አባላት ሕጉን ከአባላት ፈቃድ ውጭ  መቀየር እንችላለን ሲሉ እግዚኦ  የመብት ያለህ የተባለው "ዛሬ ሕጉን የቀየሩ የቦርድ ባለስልጣናት ነገ  ሕጉ በነሱ ላይ እንደሚያነጣጥር ይወቁ ብለን የጮህነው፣ ይህ እንዳይከሰት ነበር።" "ገንዘብ በሰላሳ  እውቀት በስልሳ " ይሏል ይህ ነው።

አባቶችን እየተጋፋ ቀሳውስቶችን እያስፈራሩ እንግሊዝኛ የማይናገር ሁሉ መሃይም ነው ሲሉ ከረሙ። ባለፈው እሑድ በሰላም ያረፉትን መንፈሳዊ አባት አቡነ  ይስሐቅን ጭምር ሳይቀር ሲዘልፍ የነበረው የቤተክርስቲያናችን ዲያቆን ጸሎትና ምህላ  የሚያስፈልገው ሆኖ  ታይቶናል። በነገራችን ላይ ጳጳሳት ከግብጽ በሚመጡበት ሰዓት አረብኛ ተናጋሪ እንዳልነበሩ ሁሉ፣ በአገራችን ያሉ የመንፈሳዊ አባቶች በግእዝ የተካኑ እንጂ ብዙዎቹ የእንግሊዘኛ ቋንቋ እንደማይናገሩ እየታወቀ ዛሬ እኔ እንግሊዘኛ በመናገሬ  ብቸኛ አዋቂ ነኝ ብሎ ሲዝናና ያየነው ዲያቆን ለድፍረቱ እግዚኦታ የሚያስፈልገው ነው። የስደት ሲኖዶስ እደግፋለሁ እያለ የአስታራቂ ለምድ ለብሶ የነበረው ይህ ዲያቆን ማንነቱን ለማወቅ ለብዙሃኑ ጊዜ  ፈጅቶ እንደሆን እንጂ እኛስ ቀደም ብለን አውቀነው ነበር። አገር ቤት ያሉ አባቶችም እያወቁ በምህረት ሲያልፉት ከርመው ሲበዛባቸው የወሰዱትን እርምጃ  ሁላችንም ያየነው ነው። ከእንግዲህ ለሰማይ ቤታችን እንጂ አላፊ ለሆነው ለአንድ ዓለም ባንጨነቅ መልካም ነው እንላለን።

ይህንን ካልን ዘንዳ በማጠቃለያው የምንናገረው አለን።

በስልጣን ላይ ያሉትን የቦርድ ባለስልጣናት የምንላቸው ነገር ቢኖር፣ ከወረዳችሁ ላትመለሱ ስለምትችሉ ሕጉን በመቀየር እራሳችሁን እድሜ ልክ ተመራጭ አድርጋችሁ እንድታስቀምጡ ነው።

ከውጭ ሲኖዶስ ጋር ከመቀላቀላችሁ በፊት የናንተን ዘላለማዊ ስልጣን እንዲቀበሉና  እንዲያጸድቁ በጽሁፍ ማረጋገጫ ብትጠይቁ መልካም ነው።

ከቤተክርስቲያኑ ስም ላይ የኢትዮጵያ የሚለውን ወደፊት ጭቅጭቅ እንዳይፈጥር አንስታችሁ በምትኩ ጁፒተር ወይም ጋርላንድ በሚል ብትቀይሩት የተሻለ  ነው። 

የእናንተን ስም  በመቅደስ የማያነሳ ካህን ካለ ማባረርን አትርሱ።

በስማችሁ ስለት የማያስገባ አባል ካጋጠመ አስወገዱ።

እናንተን የሚረዳ ከሆነ  በውስጥ ጠንካራ  ደጋፊ የሆነውን ጵጵስና አሰጡ።

የተረፈ  ገንዘብ ካለ የሚመጡት እንጋራ  እንዳይሉ በስማችሁ ሞግዚትነት ተከፋፍላችሁ አስቀምጡ።

በቤተክርስቲያኑ ውስጥ እምነት፣ መብት፣ ፍቅር፣ መከባበር የሚሉ አባባሎችን በድንጋጌ አዋጅ አግዱ።

ገንዘብ የሚከፍል ከጠፋ ከበር ላይ ደህና  ጎበዝ በማስቆም የመግቢያ ዋጋ ማሰባሰብ ጀምሩ።

የዛሬ  3  ዓመት እንደጠቆምነው ገቢው ካነሰ  ቅዳሴ  ጠበል በገንዘብ መሸጥን እንደ  ገንዘብ ማሰባሰቢያ  ተጠቀሙበት። 

የፖለቲካ አባላትን በማሰባሰብ እራሳችሁን አጠናክሩ።

ይህ ብዙውን "ችግራችሁን ይቀርፈዋል" ብለን እናምናለን።

ለሰማዩ ሳይሆን ለዚች አንድ ዓለም ምኞትም የሚያሟላ ይመስለናል። ይስመርላችሁ 11.2 ውሎ ይደር! አሜን።

ከዚህ በመቀጠል ካንባቢ የተጠቆምነውን ጽሑፍ ለእናንተ ለማዳረስ የድህረ ገጽ አድራሻውን ቀጥለን አስቀምጠንዋልና  በመጫን እንድታነቡ እንጋብዛችኋለን።

የሲኖዶስ የፈተና ጉዞ
https://docs.google.com/file/d/0B5ikXekolDC4TWplNG1yZEVUZzg/edit?usp=sharing