Saturday, March 27, 2010

መጽሐፍ ቅዱስ የጠቀሰ ሁሉ ክርስቲያን አይደለም ቁጥር ፲፱

ሳምንትም ቢቀረው ቀደም ብለን ሁላችሁንም እንኴን ለብርሃነ ትንሳኤው አደረሳችሁ ለማለት እንወዳለን። የሚመጣው ሳምንት ደግሞ ሕማማት ነውና ስቅለትን በማሰብ መረዋ ለሳምንት እንደማትታተም ከወዲሁ የምንነግራችሁ የት ጠፋችሁ? እንዳትሉን ነው። ይህንን በቤተክርስቲያናችን የተፈጠረውን ችግር ለመፍታት እስካሁን ደከመን ሳትሉ ከምእመናን ጎን በመሰለፍ የተነጠቀና የተረገጠ መብታችንን ለማስከበር በሚደረገው ትግል ተባባሪ በመሆን የምታደርጉት ተጋድሎ መጨረሻው እንደሚያምር መረዋ ጥርጥር የለውም። ከትላንትናው ዛሬ ጭላንጭልም እየታየ ያለ ይመስለናል። በስድብ አማንያንን ማናደድ እንጂ ማሰባሰብ እንደማይቻል ደግሞ በተጻራሪ ይጻፉ የነበሩት BOLGS እየተዘጉ መምጣታቸው ምስክር ይሆናል ብለን መናገር እንወዳለን። መሳደብ ለጊዜው ለሰዳቢው ያስደስት ይሆናል፡ እውነቱ ግን የሚሳደብ ሰው የሚሳደበው ይዞት የቀረበው ሃሳብ አዳማጭ አላገኘም ብሎ ሲያስብና የመጨረሻ ሽንፈት ላይ ደርሻለሁ ብሎ ድክመቱን መቀበል ሲያቅተው ብቻ ነው። ወንድሞችና እህቶች በስድብ ቢሆን ኖሮ እስካሁን በተለያየ ቦታ ብዙ ለውጥ በታየ ነበር።

ውድ አንባብያን። ባለፈው የመረዋ እትምታችን ማጠቃለያ ላይ በተጻራሪ እየተጻፉ ያሉትን የብሎጎ ጽሑፎች እንድታነቡ መጋበዛችን ይታወሳል። ምን አልባትም ክስ መመስረቱን በመፍራት ካልሆነም ብሎጉን ያስለጠፈው ድርጅት በደረሰው የሕግ ደብዳቤ መሰረት ብሎጎቹ መነሳታቸውን ለመታዘብ በቅተናል። እናንተም ለማንበብ ስትሞክሩ አጥታችሁት ከሆነ የተጻፈው በሙሉ ቅጅው ያለን በመሆኑ ለሚጠይቁን ሁሉ ለመላክ ዝግጁዎች ነን።


ብዙውን አማኝ ከምንም በላይ የሚገርመውና የሚያናድደው እንዴት ክርስቲያን እርስ በራሱ ይጨራረሳል? የሚለው ጥያቄ ነው። መረዋ ለእትምት ከበቃበት ቀን ጀምሮ በተደጋጋሚ የሚለው ነገር ቢኖር "ክርስቲያን ይፋቀራል እንጂ አይፈነካከተም፡ እዚህ እኛ አካባቢ ያለው ችግር የኃይማኖት ሳይሆን የንዋይ ፍቅርና የፖለቲካ ሽኩቻ ነው"የሚል ነበር። የኃይማኖት ቢሆን ኖሮማ:
እንደዚህ መዘላለፍ
በተለያዩ ቦታዎች እየተሰበሰቡ ሌላውን ለማጥፋት እቅድ ማውጣት፡
በስብሰባ ላይ አይደግፉንም የሚሏቸውን ግለሰቦች እንዳይናገሩ ማፈን፡ የመናገር መብታቸውን መቀማት፡
በፖሊስ ማስፈራራት፡ ብሎም ከስብሰባ ማስወጣት ባላስፈለገ ነበር።
የኃይማኖት ጥያቄ ቢሆን ኖሮማ አባላትን ለማባረር ሕገ ደንቡን ምእመናን ሳይወያዩበት መቀየር ባላስፈለገ ነበር
የኃይማኖት ነገር ቢኖርበትማ ኖሮ እንደይሁዳ መረገሚያ $30 የክርስቲያንነት መመዘኛና መለኪያ ባልሆነ ነበር።
የኃይማኖት ነገር ቢኖርበትማ ኖሮ መካሰስ ባልመጣ ነበር።
የኃይማኖት ነገር ቢኖርበትማ ኖሮ የችግሩ መልስ ከመንፈሳዊ አባቶች እንጂ ከቦርድ አባላት ባልሆነ ነበር።
የኃይማኖት ነገር ቢኖርበትማ ኖሮ ወንጌልን ያስተማሩ መንፈሳዊ አባቶች ከመንበር ባልተባረሩ ነበር።
የኃይማኖት ነገር ቢኖርበትማ ኖሮ ለቤተክርስቲያኑ የለፉት እየተባረሩ በግርግር የገቡ ግለሰቦች ለእምነታችን ተጠሪዎች ክርስቲያን ለመሆናችን አጣሪዎች አባል ለመሆን ለሚቀርብ ማመልከቻ የግለሰብ ጀርባ ተመልካቾች ባልሆኑ ነበር።
የኃይማኖት ነገር ቢሆንማ ኖሮ የቦርድ አባላት የንስሐ አባቶችን ስልጣን ለመሻማት ባልተነሱ ነበር።
ይህንን ካየን ከታዘብን በኋላ ነው የኃይማኖት ሳይሆን የቡድን የስልጣን ፍላጎት፡ የፖለቲካ ሽኩቻ ነው ብለን የደመደምነው። ወንድሞችና እህቶች ምንም የኃይማኖት ነገር በሌለበት ስለኃይማኖት መነጋገር ደግሞ እንዴት ይቻላል። እንዴው ለመናገር ያክል አንድ ቁም ነገር እናንሳ። እምነት ያለው ሰው "ወንድሞቼ እሕቶቼ ምን ሆናችሁ ብሎ ይጠይቃል እንጂ እንዴት ከቤተክርስቲያን ሕዝቡን ማባረር እንችላለን ብሎ እቅድ ያወጣል? በሚያምንና በማያምን መካከል ያለው መመሳሰል ምንድ ነው? ብሎ ለጠየቀ ሰው አንዱ ሲመልስ "ሁለቱም የቆሙለት ዓላማ መኖሩ ብቻ ይሆናል" ያለው ፈላስፋ ማን እንደሆነ ባናስታውስም እውነት ለመሆኑ ግን አባባሉ በቂ መልስ ይመስለናል።

ባለፈው እሁድ የሙዳዬ ምጽዋት ሳጥን ተሰብሮ ገንዘብ መሰረቁን የተናገሩት የቦርድ አባል ሳጥን መሰበሩንስ ይወቁ የገንዘብ መጥፋቱን እንዴት አወቁ? ብለን ተገርመናል። ሰው ያላስቀመጠውን ገንዘብ እንዴት ተሰረቀ ይላል? ከሳጥኑ የተገኘ ገንዘብ ደግሞ ለአዲስ ተመራጯ የቦርድ አባል ወይዘሮ ሰጥተናቸው ወደ ቦርዱ ጽ/ቤት ይዘው ሲወጡ አይተናል የሚሉ እህቶች መኖራቸውን ብንናገር ይክዱን ይሆን? ታዲያ ወይዘሮዋ የተረከቡት ገንዘብ ከስርቆት የተረፈ መሆኑ ነውን? የቤተክርስቲያኑስ የጥበቃ ካሜራ ያላነሳው የሰረቀው ግለሰብ ወይንም ግለሰቧ ግንዘቡን ሲቆጥር ወይንም ስትቆጥር አለማንሳቱ የቤት ሰው መሆኑን ካልሆነ መሆኗን አውቆ ይሆን? ይህንንና የመሳሰሉትን ጥያቄዎች የቦርድ አባላት መመለስ አለባቸው ብለን እናምናለን። እንዴው ለጫወታ ያክል ባለፈው ዓመት ያልተሰበረ የውስጥ በር ተሰበረ ተብሎ ፖሊስ አሻራ እንዲወስድ እንደተጠራ ሁሉ አሁንስ ገንዘብ ተሰረቀ ሲባል ፖሊስ ተጠርቶ ነበርን? እንዴው ለነገሩ ለማለት እንጂ መልሱ ጠፍቶን እንዳልሆነ መታወቅ አለበት። አንባቢያንም ጥሩ ግንዛቤ ያገኛችሁ ይመስለናል። በዚሁ እለት እኚሁ የቦርድ አባል የተሰበረው ሳጥን ቁልፉ ስለተቀየረ የምትሰጡትን ገንዘብ በፖስታ በማድረግ ሳጥኑ ውስጥ ጨምሩት እንጂ ለግለሰብ ካሁን በኋላ እንዳትሰጡ ማለቱን ስንሰማ በጣም ገረመን። ገንዘቡ ከሳጥን ሲሰረቅ እኮ ቁልፍ ነበረው የቁልፉ መቀየር መሰበሩን አያስጥለውም እንዴዉም ለግለሰብ መስጠቱ እየተመዘገበ ስለሚቀበሉት የተሻለ ይሆናል ብለን አሰብን። ካባባላቸው በመነሳት ምን አልባት የጠረጠሩት ስለት የሚሰበስቡትን ግለሰብ ነው ማለት ይሆናል ብለን ጠረጠርን። ይንን ለመቀበል ደግሞ ግራ ተጋባን ስለት ሰብሳቢውን አዛውንት ስለምናውቃቸው በገንዘብ የሚጠረጠሩ አይደሉምና። ብቻ ዘንድሮ ሁኔታዎች እየተቀያየሩ ወደ መጥፎ ገደል እየተገፋን ነው። በቃ ማለት ከመወርወር በፊት እንላለን።

በሌላ ወገን SENBETE የተባለው የቦርዱ ደጋፊዎች BLOG ባለፈው እትምቱ ላይ በመሃበረ ቅዱሳን ላይ የተወሰነ የሲኖዶስ ውሳኔ ኮፒ በማውጣት መሃበረ ቅዱሳን አገር ቤት ሳይቀር ችግር ላይ እንደሆኑ ሊያሳዩን ሞክረዋል። ለነገሩ የተባለው ውሳኔ የቆየ ከመሆኑም በላይ እነሱ ዛሬ አይተውት አዲስ ሆኖባቸው ካልተደነቁ በስተቀር እንዳሉት ሳይሆን መሃበሩ በሰንበት ትምህርት ቤት ስር እንደሆነና የኢትዮጵያ ሲኖዶስ ለመሃበሩ ልዩ ትኩረት በመስጠት በስልጣን ተዋረድ የሚሰራበትን ሁኔታ ያመቻቹበት ለመሆኑ ሙሉ ኮፒውን በማንበብ መረዳት ይቻላል እንላለን። የገረመን ሲኖዶስ አንቀበልም የሚሉት ቡድኖች ለነሱ የጠቀመ ሲመስላቸው ሊጠቅሱት ካልተስማማቸው ሊኮንኑት መሞከራቸው ነው። ወንድሞችና እህቶች የሰንበት ጸሃፊዎች። ወይ መጾም ወይ መግደፍ እንጂ እየጾምኩ እገድፋለሁ እየገደፍኩ እጾማለሁ የሚባል ነገር አለመኖሩን ማወቅ የግድ ነው ልንላችሁ እንወዳለን። የሲኖዶስ ውሳኔ ደግሞ ለሚያምን የእምነት መመሪያ ነውና ከመቀበል ባሻገር ሌላ ምርጫ ሊኖር አይችልም። አልቀበልም የሚል ቢኖር የኦርቶዶክስ ተከታይ ያልሆነ ብቻ ነው። እኛ እስከምናውቀው ድረስ ደግሞ መሃበረ ቅዱሳን ሲኖዶሱን ክደው አያውቁም። በፖለቲካ አመለካከት አመራርን መካድ ይቻላል፡ በእምነት ግን መንፈሳዊ አባቶችን መካድ የሃይማኖታችንን ምሰሶ መናድ እንደሆነ ልንገነዘብ ይገባል። መንፈሳዊ አባቶች እንደኛ ሰዎች ናቸው። በክርስቶስ የተመረጡ በመሆናቸው አባትነታቸውን ልንሳለቅበት ወይንም ልናላግጥበት አይቻለንም። ስልጣኑም ብቃቱም የለንምና። የተሳሳቱ አባቶች ቢኖሩ ሊገስጣቸው የሚችል አካል የመንፈሳዊ አባቶች ብሎም ክርስቶስ ብቻ ይሆናልና። አንዳንዴ በማናውቀው መዘባረቅ ቅስፈትን እንደሚያመጣም መጠርጠር ክርስቲያንነት ነውና ብንጠነቀቅ መልካም ነው። ካልሆነ እምነትን እንደፖለቲካ ማራመድ ካሁን የባሰ ችግር ውስጥ ይጥለንና በምድርም በሰማይም ኡኡታን ታቅፈን እንቀራለን።

በድጋሜ መልካም የትንሳኤ በዓል ለሁላችን።

በቸር ይግጠመን።

Saturday, March 20, 2010

አዲስ እረኛ ከብት አያስተኛ ቁጥር ፲፰

ይሻላታል ብለው ገዳም ቢሰዷት፤
ነካክተው ነካክተው አባባሱባት።
ብለው የተቀኙት ማን እንደነበሩ ስማቸውን ማስታወስ ተቸገርን እንጂ ቅኔው እንዳለ ትላንትና የተቀኘ ይመስል አሁንም አዲስ ነው። ቀደም ባለው ጊዜ ነው፡ {ሆይ ጉድ እኛም እንዳባቶቻችን የሰገሌ ጦርነት አቆጣጠር አይነት ቀደም ባለው ሰዓት ማለት ጀመርን፡} ወረታ በተባለው ከተማ አካባቢ የተሾመ ወረዳ አስተዳዳሪ እንኳን ወረዳ አጥቢያም ማስተዳደር እንደማይችል ሲያውቁ ያካባቢው አዝማሪዎቹ በጠጅ ቤት ስም እየጠሩ ማመሳሰል ጀምረው ምን ብለው ዘፈኑ አሉ መሰላችሁ።
ምድር እንኴን ሲያረጅ ያበቅላል እንግጫ
አቶ አበበ ነወይ የጋሽ ክፍሌ ልውጫ።
እኛም ይኸው እድሜያችን ከረመና እነ አቶ ሙሉአለም መሪዎቻችን እነ አቶ አበበ ጤፉ የኤኮኖሚ ጠበብቶች የጂኦግራፊ ምሁሮች የቤተክርስቲያን ደብተራዎች እሆኑበት ዘመን ደረስን። ነገ ደግሞ የላበኩ ዶክተር ከደጀ ሰላሙ መሬት ተጋርተው የሆነ መጋረጃ ጋርደው ነርሱን አቶ አበራን ተከተለኝ በማለት ድውያን እፈውሳለሁ ብለው ተነስተዋል ቢባል መከተል ነው እንጂ ምን ምርጫ አለን የሚለው ምእመን ይበዛ ይሆናል ብለን ብንጠራጠር የምትፈርዱብን አይመስለንም። ቤተክርስቲያናችን ከድጡ ወደ ማጡ ከገባ ቆየ። ወንድሞችና እህቶች አሁን እየተጻፈ ያለውን ብሎግ ያነበብ ሁሉ ባካባቢያችን እየተደረገ ያለውን የፖለቲካ ሽኩቻ በሃይማኖት ሽፋን እየተላለቅን ለመሆኑ ምስክር መጥራት አስፈላጊ አይመስለንም። የሚገርመው ትላንትና ከትላንት ወዲያ እንዳልናችሁ ለሕዝብ መብት እንቆማለን፤ የፖለቲካ እምነት እናራምዳለን የሚሉት ግለስቦች በጠመንጃ ያልሆነላቸውን በመስቀል ሽፋን ሊታገሉ ሲነሱ ልባቸውን አራርቶት ይሆናል ብለን የምናምን ግለሰቦች ነፃ መረማመጃ መንገድ እየከፈትንላቸው እንደሆነ አለመገንዘባችን ነው። ቤተክርስቲያን ደግሞ አምልኮ እግዚአብሄር የሚካሄድበት ቦታ እንጂ ተንኮል የሚሸረብበት ደጋፊ የሚታቀፍበት የሚጠይቅ የተቃወመ የሚባረርበት ስፍራ ከሆነ ቤተክርስቲያንነቱ ቀርቶ የፖለቲካ አዳራሽ ሆነ ማለት ነው። ዛሬም በድጋሜ እንናገር በዚህ በቤተክርስቲያን የተከሰተው ችግር የሃይማኖት ሳይሆን የፖለቲካና የጥቅም ግጭት ነው ብለን እናምናለን። ገንዘብ ሳይኖረን እንዋደድ ነበር ገንዘብ ሲበዛ ጥላችንም በዛ ማለት እውነት ለመሆኑ ማስረጃውን እያየነው ነውና።

ለውይይት እንዲመች መረዋ ዛሬ ለሁላችንም ለየት ያለ ጥያቄ ይዞ ቀርቧል

ሁላችንም ለቤተክርስቲያኑ የከፈልነው ገንዘብ ስንት ነው? በጉልበት ምን አድርገናል? ብለን እራሳችንን እንጠይቅና ከመልሳችን በመንደርደር ወደቀጣዩ ነጥብ እናዝግም። ይህ ደግሞ ቤተክርስቲያኑ ከተጀመረበት ወቅት ጀምሮ ያዋጣነውን፡ ያደረግነውን ሁሉ ያጠቃልላል። አንድ ድርጅት ሲቌቌም የባለቤትነት ጥያቄን የሚመልሰው የመስራች አባላት ስብስብ ነው ብለን ስለምናምን። በመሆኑም በእኛ የማስታወስ አቅም አንዳንዶቹን እናንሳ። በገደፍነው ሞልታችሁ የተረሳውን አስባችሁ አንብቡት ለማለት ነው።
አቶ ሰይፉ ይገዙ፦ ይህንን ቤተክርስቲያን በገዛንበት ወቅት የተጫወቱትን ሚና ሊክዱ የሚችሉት ዶክተሩና ደጋፊዎቻቸው ሊሆኑ ይችላሉ ብለን እንጠረጥራለን። ካልሆነ ቤታቸውን አሲዘው matching grant አስገኝተው ሕልማችን እውን እንዲሆን ያደረጉ ግለሰብ ለመሆናቸውና ለዚህ ቤተክርስቲያን የተቻላቸውን ለማድረጋቸው መመስከሩ እኛን ያስደስተናል እንጂ አያስፈራንም።
አቶ ሃይሉ እጅጉ ከጀማሪዎች አንዱና ከማንም በላይ ለቤተክርስቲያኑ ገንዘባቸውን የለገሱ በአርአያነት ሊጠቀሱ የሚችሉ ግለሰብ በተመራጭነት ያገለገሉ።
አቶ እዩኤል ነጋ ከአመሰራረቱ ጀምሮ ጉልበታቸውን ጊዜአቸውን ገንዘባቸውን ለቤተክርስቲያኑ ያዋሉ ግለሰብ ለመሆናቸው ምስክር የሚያሻ አይመስለንም።
አቶ ምናሴ በየነ የቤተክርስቲያኑ ጀማሪ በጉልበት በገንዘብ ከሁሉም የማይተናነስ አስተዋጽኦ ያደረጉ።
አቶ ኪዳኔ ምስክር ከጀማሪዎቹ አንዱና በጉልበት በጊዜአቸው በገንዘብ ከማንኛችንም በላይ መስዋእትነት የከፈሉ። ሲሰድቧቸው የሚስቁ ሲገፏቸው ይቅርታ የሚጠይቁ። {የባለቤታቸውን ተሳትፎ ሁሉም የሚያውቀው በመሆኑ መናገር ደግሞ ቡራኬያቸውን መጋራት እንዳይሆን እንሰጋለን።}
ወይዘሮ ሃይማኖት በየነ የአቶ ኪዳኔ ምስክር እናት፦ ይህ ቤተክርስቲያን ሲመሰረት ያንገታቸው ወርቅ ሳይቀር አውልቀው በመሸጥ ለቤተክርስቲያኑ ያበረከቱ። ጊዜአቸውን ንብረታቸውን ያፈሰሱ።
ዲያቆን አርአያ ኃይለመስቀል {በዚህ አጋጣሚ የቤተክርስቲያኑ መስራች የነበሩትን እናታቸውን ወይዘሮ የሺሃረግ ወልደጊዮርጊስን ማስታወስ ተገቢ ይመስለናል}በድቁና በተመራጭነት በገንዘብ ከማንም ባላነሰ ያገለገሉ የከፈሉ።
አቶ ዬሴፍ እረታ በጀማሪነት ብሎም በተመራጭነት ያገለገሉ አሁንም በማገልገል ላይ ያሉ።
ዲያቆን ጌታቸው ወልደሚካኤል በድቁና በተመራጭነት በገንዘብ ቤተክርስቲያኑን ያሳደጉ።
አቶ ጌታቸው ትርፌ ከመስራቾች አንዱ ሆነው በተመራጭነት ለማገልገል ፈቃደኛ ባይሆኑም በኮሚቴ ውስጥ ያገለገሉ ገንዘባቸውን ጊዜአቸውን የሰው። {ባለቤታቸው ተመራጭ ሆነው ማገልገል ብቻ አይደለም በኮሚቴ ውስጥ ያገለገሉ መሆናቸውን መጥቀስ ያስፈልጋል}
አቶ ብዙአየሁ ጌታቸው በተመራጭነት አሁንም እያገለገሉ ያሉ ከመሆናቸውም በላይ ምናልባትም ከማንኛችንም ባላነሰ ገንዘባቸውን ያበረከቱ ጊዜአቸውን የለገሱ መክፈላቸው እንዳይሰማ ይደብቁ ስለነበር በመናገራችን ሐጥያቱን እኛ ተቀብለን በንስሃ ልናወርድ እንሞክራለን።
አቶ ጸሃይ ጽድቅ ቤተማርያም ለቤተክርስቲያኑ መሰቀሎችን ንዋዬ ቅዱሳትን በማቅረብ በቤተክርስቲያኑ ውስጥ የሚበሩትን 24 መብራቶችን ያበረከቱ በገንዘብ ቤተክርስቲያኑን የደጎሙ።
ወይዘሮ በየነች መኮንን እኝህ እናት ለወጣት ልጆቻችን ካላቸው ፍቅር ለታዳጊ ወጣቶች ያበረከቱት ግልጋሎት የማይረሳ ከመሆኑም በላይ በተመራጭነት በኮሚቴ ተወካይነትያገለገሉ።
አቶ ታደሰ ጸሃዬ በገንዘብ በጉልበት ከማንም ባላነሰ ለዚህ ቤተክርስቲያን አስተዋጽኦ ያደረጉ።
ዶክተር አምሃ ኃይለመስቀል በገንዘብ ብሎም የዘማርያንን አልባሳት ወጭ በመሸፈን በጉልበት ሁሉ ያገለገሉ።
አቶ አጽቀ ግርማ የድሮውን ቤተ ክርስቲን አጥር ለማሳጠር የወጣውን ወጪ በግላቸው የሸፈኑ ከማንም ያላነሰ የገንዘብ መዋጮ ያደረጉ።
ዶክተር ግርማ በቀለ በተመራጭነት ያገለገሉ በገንዘብ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረከቱ።
አቶ ዳኜ ላቀው በተመራጭነት በሽማግሌነት ያገለገሉ።
አቶ ግርማቸው አድማሴ በገንዘብ በተለይም ቤተክርስቲያኑን ከችግር ለማዳን መተዳደሪያ ደንቡን እንዲያጠና የተቌቌመውን ኮሚቴ በሰብሳቢነት በመምራት ትልቅ ተጋድሎ ያደረጉ።
አቶ ዳዊት አለማየሁ በተመራጭነት በገንዘብ ቤተክርስቲያኑን የረዱ ሌት ከቀን ደከመኝ ሳይሉ ምንም ቀን ከመቅደሱ በር ሳይለዩ እያገለገሉ ያሉ አርአያ ሊሆኑ የሚችሉ ግለሰብ ናቸው።
አቶ ኪዳኔ በየ በተለያየ ወቅት ገንዘባቸውን መኪናቸውን ሳይቀር የለገሱ።
አቶ ኤልያስ ገ/ስላሴ በተጠየቁ ሰዓት ሳይሆን ሳይጠየቁም ለቤተክርስቲያን መለገስን እንደ ባህል የወሰዱ የውጭ መብራቶችን አሰርተው ያመጡ መኪና ሳይቀር የለገሱ በኮሚቴ ተመራጭነት ያገለገሉ።
ወይዘሮ ፍኖት ጋሻው ለቤተክርስቲያናችን እድገት ትልቅ አስተዋጽኦ ያደረጉ በዘማሪነት በተለያዩ ኮሚቴዎች ያገለገሉ በአርአያነት የሚጠቀሱ አኩሪ እናት ናቸው። [ባለቤታቸው ዲያቆን በላይ በችግሩ ጊዜ በድቁና ቤተክርስቲያኑን ሲያገለግሉ የነበረ፡ በተመራጭነት ይህንን ቤተክርስቲያን እዚህ ካደረሱት ግሰቦች አንዱ ናቸው።
ወይዘሮ ገነት ከበደ በገንዘብ በኮሚቴ አባልነት ደከመኝ ሳይሉ ይህንን ቤተክርስቲያን ከልባቸው ያገለገሉ።}


እነዚህና እናንተ የምታውቌቸውን ግለሰቦች ሰብስበን ለምን ይህ ቤተክርስቲያን ተቌቌመ? አላማችሁ ለፖለቲካ ተወካዮች አሳልፎ ለመስጠት ነበረ ወይ? ባቌቌማችሁት ቤተክርስቲያን ወሳኙ ሕዝብ መሆን ይኖርበታል ብላችሁ ታምናላችሁ ወይንስ በጉልበት ሕጉን ቀይሮ አማኞችን እያባረረ ክርስቶስን ሳይሆን የኛን የበላይነት መቀበል አለባችሁ የሚለውን ፈላጭ ቆራጭ ቦርድ? ቅንጅት ሆኖ ክርስቲያን ኢሕአፓ ሆኖ አማኝ ኢሰፓ ሆኖ ቆራቢ ኢዲው ሆኖ ደብተራ የሆነ እንዳለ ሁሉ በፖለቲካ የማያምን ግለሰብ ወይንም ኢትዮጵያ ያለውን መንግስት የሚደግፍ የኦርቶዶክስ አማኝ አለ ብላችሁ ታምናላችሁን? ካልሆነ እንደ ክርስቲያንነታችሁ ብቻ ሳይሆን እንደ መስራች አባልነታችሁ ለተደነቀረብን ችግር ለተፈጠረው ፈተና ምላሻችሁ ምንድነው? የቤተክርስቲያኑ የወደፊት ጉዞ ካላማረን ያዋጣነውን ድርሻችንን የመካፈል ጥያቄ ማቅረብ ቢጀመር መልሳችሁ ምን ይሆናል?
ግማሾቻችሁ ከሳሽን እንጎዳለን ብላችሁ ያወጣችሁት መተዳደሪያ ደንብ ዛሬ እናንተንም አላላውስ ማለቱን ስታዩ ምን ተሰማችሁ?
ቤተክርስቲያናችን ከሰሱ በሚባሉት ሰዎች ነው ወይንስ በነሙሉዓለምና በምሁራን ተመራጮች ነው እየፈራረሰች ያለችው?
አበበ ጤፉ ሰላም ፈጣሪ፡ ዲያቆን አርአያ ቤተክርስቲያን በታኝ።
ሙሉአለም ክርስቲያን፡ ዲያቆን ጌታቸው ከሃዲ።
ዶክተር ግርማ ታማኝ፡ አቶ ተኮላ ዘራፊ።
አበራ ፊጣ ጸሎተኛ፡ አቶ በቀለ አስመሳይ።
ወይዘሮ ሰሎሜ መንፈሳዊ፡ ወይዘሮ ጥሩአየር ዓለማዊ። ናቸው ብላችሁ ታምናላችሁን? የነዚህን መልስ ከመለሳችሁ ችግሩ በቀላሉ ይፈታል ብለን እናምናለን።

ብዙዎቻችሁ አቌም ለመውሰድ የተቸገራችሁት ለምን ይሆን? ለሚባል ጥያቄ ብዙዎች ምእመናን ሲመልሱ ምንአልባት የላበኩ ዶክተር ያገኙባቸው መረጃ ቢኖር ይሆናል እንጂ ቢናገሩ የሚሰሙ ግለሰቦች ዝም ማለት አልነበረባቸውም የሚለው አባባል የከተማ መወያያ ነጥብ መሆኑን ሳትሰሙ የቀራችሁ አልመሰለንም። ችግር ፈጣሪዎቹ ከሳሾች ናቸው ከተባለ ከዶክተሩ ጋር በመቆም፡ የለም የከሳሾች ጥያቄ የመብት ጥያቄ ነው ብላችሁ ካሰባችሁ ደግሞ ከከሳሾች ጎን በመሰለፍ አስቸኴይ የሆነ መፍትሄ ማምጣት ስትችሉ ዝምታው ለምን እንደሆነ ሁሉንም ግራ ያጋባ ጉዳይ ነው። መተዳደሪያ ደንቡን የቀየርነው ለክስ መርቻ እንጂ ለዘለቄታ መፍትሄ ነው ብለን አልነበረም የሚሉት የትላንታና የቦርድ ተመራጭ የነበሩት እመቤት ስህተተ መሰራቱን ለመቀበል ዳር ዳር የሚሉ ይመስላል። ታዲያ እሳቸውን በድጋሜ ማስመረጥ ያቃታቸው ባለቤታቸው እንደውድ ባለቤታቸው ትላንት ተሳሰቼ ነበር ብለው ቢነሱ ምናልባት አንሰማህም ያላቸው ምእመን እንደገና ጆሮ ይለግሳቸው ይሆናል ብለን እናስባለን።
በእኛ እምነት ክርስቲያንን የሚያስፈራው ምንም ነገር ሊኖር አይችልም ብለን እናምናለን። የመጨረሻ ማስፈራሪያ ሞት ሆኖ ሳለ ክርስቲያን የሆነ ሁሉ ደግሞ በትንሳኤ ያምናልና። ስለዚህም ነው እውነትን ክዶ ከመኖር ለእውነት መሞትን መምረጥ ይሻላል የምንለው። ካልሆነ ግን በአዲስ መንፈስ ባዲስ ጉልበት ሊበታትኑን የተነሱት የቦርድ ተመራጭ ነን ባዬች ሳይበታትኑን እንደማይተኙ እመኑ። በርእሱ ላይ አዲስ እረኛ እንቅልፍ አያስተኛ የተባለውም ለዚህ ነው። በዚህ አጋጣሚ ነገሩ አንገብግቧችሁ እየተፋለማችሁ ያላችሁትን ስም እየተሰጣችሁ መሰደባችሁን ሳይሆን የተነሳችሁበትን አላም መወንጀላችሁን ሳይሆን እምነታችሁን ይዛችሁ ያላችሁትን ሁሉ ማመስገን እንወዳለን። የመረዋ ሃሳብ እንቅልፍ የነሳቸው ደካሞች መረዋ በሚል ሌላ BLOGS ከፍተው እየጻፉ እንደሆነ ባለፈው ነግረናችሁ ነበር። እባካችሁ ገብታችሁ አንብቡላቸው። ያንን ካላነበባችሁ ድክመታቸውን ልትገነዘቡት አትችሉም። እነዚሁ ግለሰቦች SENEBETE በሚልም ስያሜ ስለሚጽፉ ገብታችሁ እንድታነቡላቸው እንለምናችኋለን እዳሪና አፈር የሚለየው በሽታው ነውና።

Monday, March 8, 2010

ጣር የያዘው ሲንፈራገጥ ላላወቀ የሚራገጥ ይመስላል። ቁጥር ፲፯

እንዴት ከረማችሁ? ባልን ቁጥር የግላችንን ካልሆነ በስተቀር በቤተክርስቲያናችን የሚደረገውን ሽኩቻ ከሆነ የምትጠይቁን መልሱን ፈጣሪ አምላክ ይፍታው እያልን ነው ያለነው ትሉን ይሆናል። እኛም ከናንተ የተለየ መልስ የለንም። ባለፉት ሁለት ሳምንታት፤ በየብሎጉ የተጻፉትን የሐሰት ውንጀላዎች፤ ስም ማጥፋቶች፤ ስድቦችና ማስፈራሪያዎች ያነበበ ሁሉ አገር ለመልቀቅ ከተማ ለመቀየር ቢያስብ አይፈረድበትም። ከውሸትም እኮ እውነት የሚመስል ውሸት አለ። የነዚህ ግን ዓይን ያወጣ ሃሰት ሆነብን። በቅሎ ትወልድ ይሆናል ብሎ መጠራጠርና በቅሎ ስትወልድ አየሁ ማለት የተለያዩ ናቸውና። ለነገሩ ስማቸው በሃሰት የጠፋው ግለሰቦች በሕግ በደላቸውን ለመበቀል በመነሳት አስፈላጊውን ሕጋዊ መንገድ እያጣደፉት በመሆኑ በቅርቡ ይፋ የሚሆን ለሁላችንም ትምህርት ሊሆን የሚችል የሕግ መፍትሄ እንደሚኖር ተጠግተው ያዳመጡ ሁኔታውን የተከታተሉ አስተማማኝ ምንጮች ሹክ ብለውናል። ይህንን ስንሰማ አልተደሰትንም ሁኔታዎች ከቁጥጥር ውጭ እየሆነ መሄዱን ተገነዘብን እንጂ። ቀልደኛው ጔደኛችን ምን ትቆዝማላችሁ "ምከረው ምከረው ካልሰማ መከራ ይምከረው"ይባላል እኮ። እንዴውም ሰሞኑን የደረሰኝን ቀልድ ልንገራችሁ አለና የሚከተለውን አጫወተን። "አንድ አስተማሪ ስለ አሳነባሪ ሲያስተምር አሳ ነባሪ ሰውን መዋጥ አይችልም ምክንያቱም አፉ ሰፊ ቢሆንም ጉሮሮው ጠባብ ነው ብሎ ሲያስተምር አንድ ወጣት ተነሳችና በመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርታችን ላይ በአሳ ነባሪ የተዋጠውን ዮናስን መንግስተሰማያት ሳገኘው እጠይቀዋለሁ። ብላ ላስተማሪዋ ነገረችው። አስተማሪውም በሹፈት መልክ ዩናስ ገሃነመ እሳት ገብቶስ ከሆነ?ብሎ ሲጠይቃት ሲኦል ከገባም ችግር የለውም አንተ ትጠይቀዋለህ ብላ መለሰችለት።" ብሎ አሳቀን። የታሪኩ መልእክት እምነትን የሚመለከት ነው። ማብራሪያ የሚያሻው አልመሰለንም።

እድገትን መቀበል መልካም ነው። እድገት ደግሞ በተለያየ መልክ ይገለጣል። ባካባቢያችን ያሉ ወጣቶች የሚናገሩትን በመስማት የተቀየረውን አማርኛ ማጣጣምና ምን ማለት ነው? ብሎ መረዳት የግድ ሆኗል። "ይመችህ" የሚለው አባባል ምን ማለት እንደሆነ ለማወቅ ሌላ ወጣት መጠየቅ መሃይም መሆን አይደለም። እኛ የምናውቀው አማርኛ ቀስ በቀስ እየተቀየረ ነው። እንደትላንትናው "እኔ አላምንም" የሚለው የአነጋገር ዘይቤ ተቀየሮ ዘንድሮ "እንዲህማ አትለኝም" "እንደሱማ አታረገኝም" ሲሉ መስማት ለኛ እንግዳ ይሆን ካልሆነ በስተቀር ለወጣቶቹ ትክክለኛ ቌንቌ ነው። ለነገሩ ይህንን ያነሳነው ቌንቌና የቌንቌ ግንዛቤ የባህል ክፍል ነውና ከአዲስ መጤው ቌንቌ ጋር እየተካለስ የተለየ የራሱን እድገት እንደሚመራ ለመጠቆም ያክል ነው። ሃይማኖትም ይህ እንዳይደርስበት ቀንና ሌሊት መታገል ሊኖርብን ነው። በተለይ የኛ የኦርቶዶክስ እምነት እስካሁን ጠብቆ የቆየውን መለያ እንዲያጣ የሚደረገው ትግል ከፍተኛ ነው። ይህ ትግል ደግሞ ከውጭ ብቻ ሳይሆን ከውስጥም ለመጧጧፉ እሩቅ መሄድ አያስፈልግም። "ማርያም አታማልድም " የሚሉ ድሮ ተወግረው ተገድለዋል። ዛሬ ታማልዳለች ብለን የምናምነውን ሊወግሩን ተነስተዋል። "ሁለትም ሶስትም ሆናችሁ በተገኛችሁበት ሁሉ እገኛለሁ" ያለውን ቃል ዘንግተው። እጅ ለእጅ ተያያዘው እየጸለዩ: በጋራ እየለመኑ፡ እኔ ጸልዬ አድንሃለሁ እያሉ ይቆዩና የማሪያም ምልጃ ሲነሳ ግን ያንገፈግፋቸዋል። "አንቺ ሴት ቀኔ አልደረሰምና አታስቸግሪኝ"ሲል ቆይቶ "ያላችሁን አድርጉ"በማለቷ ውሃውን ወደ ወይን የመቀየሩን የቃነ ዘገሊላውን ተአምር ሲያነሱባቸው ፊታቸውን ያዞራሉ።

ወንድሞችና እህቶች ጾም በአዋጅ ቢነሳ ደስ የሚለን ብዙዎች ነን። ግን አይሆንም። ቅዳሴ በመኪናችን ወስጥ ባለ ካሴት አዳምጠን ቤተክርስቲያን ከመሄድ ብንቀር የምንፈልግም እንኖራለን። ከነጫማችን የቤታችንን ወለል ለመርገጥ ተጠይፈን ለምን ቤተክርስቲያን ጫማ እናወልቃለን የምንል ብዙዎች ነን። በፈቃድ የምናደርገውን እንደ ትእዛዝ የምንወስድም ብዙዎች ነን። ያገር ልብስ መልበስ አላዋቂነት ከረባት ማሰር የምሁርነት መለኪያ የሚመስለን ብዙዎች ነን። ይህ ካለማወቅ የመጣ በመሆኑ ማንም ማንንም መንቀፍ የለበትም። የኦርቶዶክስ እምነት ኋላ ቀር ነው የሚሉ ሰባክያን ከውጭ ብቻ ሳይሆን ከውስጥም ለመሆናቸው የሚከተለውን በመጫን የተቀረጸውን ተመልክተው የራስዎን ግንዛቤ ይውሰዱ።


ይኸንን ልናነሳ የወደድነው እናንተን ለመስበክ ሳይሆን አንዳንዴ ምን እየተደረገ ነው የሚለውን ማዳመጥ ጥሩ ነው ብለን ስለምናምን ነው። አዲሶች የቦርድ ተመራጮችና በጣት የማይቆጠሩ ደጋፊዎቻቸው ከኛ የተለዩትና ጠንካራ የሆኑት እኛ ፈጣሪን ስለምንፈራ አባቶችን ስለምናከብር ወጣቶችን ስለምናዳምጥ ሲሆን እነሱ ግን ከራሳቸው በስተቀር የሚያከብሩትም ሆነ የሚፈሩት ምንም ነገር ስለሌለ ነው። ከሁሉ በላይ የሚያስፈራ ጠላት ደግሞ ምንም አይነት እምነት የሌለው ነው ይላሉ። ባይሆንማ ኖሮ ሽማግሌዎች ሲያናግሯቸው፡ ምእመናን ሲለምኗቸው፡ ከመሳደብ ይልቅ ማዳመጥን በወደዱ ነበር። በግል አነሳሽነት የቤተክርስቲያኑ ጉዳይ ያሳሰባቸው ግለሰቦች የከሳሽን ቡድን ክሁለት ጊዜ በላይ የቦርድ አባላትንም እንዲሁ ማነጋገራቸውን ሰምተን ነበር። አሁን የደረሰን ዜና ደግሞ አማራጭ ነው የሚሉትን ሃሳብ ለከሳሽም ለቦርድ አባላትም ማቅረባቸውን ነው። ያቀረቡት ሃሳብ ቅጂ ሲደርሰን ለናንተ ለማቅረብ ቃል እየገባን ባላየነው ሃሳብ ላይ ለዛሬ አስተያየት ከመስጠት እንቆጠባለን።

እንዴው ለፈገግታ እንዲሆንላችሁ በቤተክርስቲያን አካባቢ የተባለውን እንንገራችሁ። የቀድሞው ሊቀመንበር ካንድ የቦርድ አባል ጋር ስለ አጀንዳ ሲወያዩ የቦርዱ አባል የቀድሞውን ሊቀ መንበር "መቼ ነው ይህንን ደግሞ የወሰንነው?" ብሎ ቢጠይቀው "ወንድሜ ዘንድሮ እኮ እኔና ተዋበች ማለት የቀድሞው ብዙአየሁና ሰሎሞን ማለት ነን አለ ብለው ነገሩን" በሰፈሩት ቁና መሰፈር ይሏል ይኸ ነው።

የቀድሞው የቦርድ ተመራጭ የነበሩትና ከስልጣን በምርጫ የተሸነፉት ዓመቱን ሲጨቃጨቁ የከረሙበትን አይምሯቸውን ለማዝናናት በሚቀጥለው ወር ከባለቤታቸው ጋር ለአንድ ወር ወደ ኢትዮጵያ እንደሚሄዱ ስንሰማ አይ ጉዳቸው ጉዞአቸውን ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር ያገናኙና መከራቸውን ያሳዩአቸዋል ብለን ለነሱ እኛ አዘንን። እነሱ ትላንት ሌላውን እንዲያ ማለታቸውን ዘንግተን አይደለም፡ ግን ዘንድሮ እኮ አገርቤት ገብቶ መምጣት ወንጀል ነው ብለው የሚሰብኩን ደግሞ እየተመላለሱ ያሉት የፖለቲካ መሪዎች ናቸው። ስም እንጥቀስ እንዴ? የለም እኛ ከነሱ በላይ ሆነን መገኘት እንፈልጋለን። እነሱ ይሳደቡ፡ ያላደረግነውን አደረጉ ብለው ይወንጅሉን፡ እኛ ይቅር በላቸው ብለን እንጸልይላቸዋለን።

አንድ ልጅ እናቷን "እማማ ለምን ጸጉርሽ ሽበተ ጀመረው? ብላ ትጠይቃለች አሉ እናትየዋም "ልጄ አንቺ ያመጣሽብኝ ጣጣ ነው ባናደድሽኝ ቁጥር በዋሸሽኝ ቁጥር ሽበቴ ይጨምራል" አለቻት ልጅቷም አሰበችና ታዲያ ያያቴ ፀጉር ለምን ሁሉም ነጭ ሆነ? ብላ ደግማ እናቷን ጠየቀች ይላሉ።

በሚቀጥለው እትማችን የአማርጭ ፈላጊ ቡድንንና የሰላም ፈላጊን ተመራጮች የደረሱበትን ጠይቀን ልንነግራችሁ ቃል በመግባት እነሰናበታችሁ። ቤተክርስቲያኑ እንዳይፈስ የምንታገለው እኛና እናንተ መፍረሱን ለማጣደፍ የሚራወጡት ደግሞ የቦርዱ ተመራጮችና በጣት የማይቆጠሩ አፈ ጮሌ ደጋፊዎቻቸው መሆናቸውን አትዘንጉ። ሁላችንም ላመንበት ከቆምን ለውጥ እናመጣለን ብለን እናምናለን።
ደህና ሁኑ።
















የሰላም ኮሚቴ የደረሰበትንና የአማራጭ ሰጪ ኮሚቴ

Monday, March 1, 2010

አዋጅ በሰማን ቁጥር መጥፎ ትዝታን ይቀሰቅስብናል። ቁጥር ፲፮

ቆየት ብሏል ዘመኑ ታሪኩን ያጫወቱኝ ዘመዴ ዛሬ በሕይወት የሉም። መሬቱን ገለባ ያድርግላቸው። ብዙ ታሪክ ይነግሩኝ ነበር። ታዲያ ቀደም ባለው ዘመን ወሎ ተፈጸመ የተባላውን ሲያወጉኝ እንዲህ አሉ። "በወቅቱ ክርስቲያን የሆነ ሁሉ በግንባሩ ላይ በእጁ ላይ መስቀል ተነቅሶ ወይንም ማተብ አስሮ መስቀል ባንገቱ አንጠልጥሎ በመንቀሳቀስ ማንነቱን ሲያስመሰክር፤ እስላሙ ደግሞ ጉፍታ በመከናነብ የስላም ኮፍያ በማጥለቅ ማንነቱን ያሳውቅ የነበረበት ወቅት" እንደነበር ነገሩኝ፡፡ "በጊዜው የሃይማኖቱ ልዩነት እየገፋ መጣና እርስ በእርስ መገዳደል ተጀመረ። ታዲያ ሁሉም እየተፈራራ ባለበት ሰዓት በመንገድ ላይ ሁለት ሰዎች ተገናኙ። ሁለቱም የመስቀል ምልክት አልነበራቸውም ወይንም የእስላም ኮፍያ አላጠለቁም ነበር። ከሁለቱ አንደኛው ጎራዴ ካፎቱ አወጣና ሌላውን እስላም ክርስቲያን? ብሎ ጠየቀው የግለሰቡ መልስ ምን ነበር መሰላችሁ "ሃይማኖት የለኝም"የሚል ነበር"። ግለሰቡ ይህንን ያለው ጎራዴ ያወጣበት ሰው ሃይማኖቱ ምን እንደነበረ መናገር ስላልቻለ እንደነበረ ለመረዳት እንችላለን። ይህንን ያጫወተን እንደ አቶ ሐዲስ ዓለማየሁ የፍቅር እስከ መቃብር ጉዱ ካሳ ከመሃከላችን ሁኖ እየተናገረ የሚያስቀን በቀልድ ቁምነገር የሚያስተላልፈው አባላችን ነው።
ዘንድሮም በከተማችን የእየተከሰተ ያለው እንዲሁ እየሆነ እየመጣ ነው። የሚካኤል ቤተክርስቲያን አባል ነህ አይደለህም? ሲባል በኦርቶዶክስ እምነት የተጠመቅሁ ቤተክርስቲያኑ ሲሰራ ካለኝ ቆንጥሬ አነሰ ሲሉ በወር ከፋፍዬ የምችለውን የሰጠሁ፡ በየጊዜው ከቅዳሴ በኋላ ሙዳዬ ምጽዋት ሲዞር የለገስኩትን ማወቅ ያለበት ሚካኤል ብቻ ነውና ጠቅልዬ እሰጥ የነበረ መሆኔን የሚያውቅ ያውቀዋልና ምስክር መጥራት የለብኝም የሚሉ ብዙ ናቸው። አባል ነኝ ብዬ አምናለሁ እነደትላንትናው በአቶ ሙሉዓለም ከቅዳሴ በኋላ በታወጀው አዋጅ አይደለህም ቢሉኝ ደግሞ አልገረምም የሚሉ ደግሞ እንዳጋጠሟችሁ እርግጠኛ ነን። አቶ ሙሉዓለም ያወቁ መስሏቸው ከመቅደሱ ፊት ቆመው "እኛ ሕዝብን ለማስደሰት በሕዝብ ግፊት አንሰራም በሕጋችን መሰረት ለ 6 ወር የአባልነት ክፍያ ያልከፈለ ሁሉ $50 የመመዝገቢያ ከፍሎ ማመልከቻውን ቦርዱ ካየውና ካጠናው በኋላ አባልነቱን እንፈቅድለታለን ወይንም እንከለክለዋለን" ብለው ያወጁትን አዋጅ ከሰሙ በኋላ የተባለውን ነው የምናጫውታችሁ። አዋጁን ስንሰማ እኛንም የቀድሞውን አሰፋ ይርጉን አስታወስን። የሳቸው ከዛኛው የሚለየው ድምጻቸውና ያነባበብ ችሎታቸው ብቻ ነበር። ቤተክርስቲያን የቤት ክፍያ እንዳቃታቸው ግለሰቦች አባላትን በገንዘብ ተመን ስታስወጣ ማየትን የመሰለ ምን የሚያሳዝን ነገር አለ። የሚገርመው አዋጁ የተነበበው ሊያስቀድስ ለመጣው ሕዝብ መሆኑ ነው። ከርስቲያን ሆነህ የምንልህን ካልከፈልክ አባል አይደለህም ይሉና የሚናገሩት አባል ለሚሉት ሳይሆን በእንግድነት ለመጣው ሕዝበ ክርስቲያን መሆኑ ነው። አቶ ሙሉዓለም ወይ የኦርቶዶክስ አማኝ ሁሉ ወንድምና እህታችን ነው ይበሉ ካልሆነ ለጥቂት ደጋፊዎቻቸውና አባላትለሚሏቸው በፖሰታቤት ልከው አዋጁን ተፈጻሚ ያድርጉት። ሁለት መርጦ አይሆንም። ገንዘብ የለንም ነገር ግን ትምህርት ቤት እናሰራለን። ገንዘብ የለንም ነገር ግን አስተማሪ እንቀጥራለን። ገንዘብ የለንም ነገር ግን የመኪና ማቆሚያ እንጠግናለን። ገንዘብ የለንም ጣራውን እናሰራለን ቀለሙን እንቀባለን። ገንዘብ የለንም ዶክተሩን ለቤተክርስቲያን አስተዳዳሪነት እነቀጥራለን ይህንንም በቆዩ የሽማግሌ አባላት በኩል ተፈጻሚ እናደርጋለን ካላደረጉ በተካንንበት ዘዴያችን ስማቸውን እንበክላለን ወይም እንደልማዳችን በደጀሰላም ቀርበን እናስፈራራቻዋለን። ሲሉ ይቆዩና የምንችለውን እንክፈል የሚሉትን ምእመናን ደግሞ እኛ ያልነውን ካልከፈላችሁ ገደል ግቡ ሲሉ እንሰማለን።
ይህ እንደሚመጣ ደግሞ ቀደም ብለው የነገሩን ግለሰቦች ነበሩ። መቼም ትንቢተኛ ባገሩ አይከበርም ሆነና ያዳመጥናቸው ግን ጥቂቶች ነበርን። ዛሬ ደስተኛ የሆንነው ትላንት ቤተክርስቲያናችንን ሊያፈርሱ ተነስተዋል ይሏቸው የነበሩትን ግለሰቦች ይቅርታ አድርጉልን ቤተክርስቲያናችንን የምታፈርሱት እናንተ ሳትሆኑ እነዚህ በቡድን ቦድነው የተመረጡት አንባ ገነኖች መሆናቸውን ደርሰንበታል ሲሉ ስንሰማ ነው። ሰው አይሳሳትም አይባልም ትልቅነቱ የሚለካው ነገሩ ሲገባው ይቅርታ እውነቱ አሁን ተገልጾልኛል ሲል ነው።
የዚህ ቤተክርስቲያን ችግር $30 በመክፈልና ባለመክፈል ነው የሚል ሰው ካለ እንደገና እራሱን መጠየቅ ይኖርበታል። የ $30 ብር ክፍያ ሳይመጣ በፊት ይህ ቤተክርስቲያን ብዙ ገቢ ነበረውና። ገንዘባቸውን ለቤተክርስቲያኑ ያፈሰሱት ደግሞ የዛሬዎቹ ተመራጮች በፈጠሩት ደባ የተናደዱና መክፈላቸውን ያቆሙ አባላት እንጂ ከተመረጡት ውስጥ ምናልባት ካንዱ ግለስብ በስተቀር በልገሳ አይጠረጠሩም አይታሙም። ለዚያውስ ቤተክርስቲያኑ ተገዝቶ ተከፍሎ ያለቀው ዓምና እነዚህ ዛሬ የሚያምሱን ተመራጮች የተቀላቀሉን ትላንትና።
መንገድ ዳር ተቀምጦ የሚያለቅስ ልጅን አይቶ ምንሆንክና ታለቅሳለህ ቢለው?ነገር ከሆዴ ገብቶ እየተናደድኩ ነው። እንጀራ እናቴ ከመምጣቷ በፊት እረሃብ ምን እንደነበር አላውቅም ነበር አሁን ግን መራብ አይደለም እራበኝ ሲሉ እየቀለድሁ ያለፍኴቸውን ሰዎች እያሰብኩ ጭምር ነው የማለቅሰው አለ ይሉ ነበር። 20 ዓመት በሰላም የተቀመጠ ህብረተሰብ በጥቂቶች በቅርብ ጊዜ ታምሶ እዚህ መድረሱ የሚያሳዝን ነው። የነዚህ ግለሰቦች ሕልም እውነት የሚሆነው፡ "የኦርቶዶክስ እምነትን ከተቻለ ማጥፋት ካልሆነ መከፋፈልና መሸርሸር "የሚለውን ዓላማቸውን ማኮላሸት የሚቻለው አሁንስ በቃ ማለት ስንችል ብቻ ነው። ለዚህ ደግሞ መካሪ አነሳሽ አያስፈልገንም። የምእመኑን ጉልበት የምእመናኑን ታጋሽነት እንዳለማወቅ የወሰዱት የቡድን ተወካዮች ትምህርት ሊያገኙ የሚችሉት ውሸት በቃን የተነጠቅነውን ሕብረት መመለስ መቻል አለብን ቤተክርስቲያኑ ንብረታችን ነው ማለት ስንችል ብቻ ነው።
ከሁሉ የሚገርመው አዲስ የያዙት ፈሊጥ የራሳቸውን ልጆች ከቤተክርስቲያንችን እያሸሹ በልጆቻችን ስም የአዞ እንባ እያለቀሱ መነሳታቸው ነው። አባቶቹንና እናቶቹን እያባረሩ ልጆቹን እንፈልጋለን ማለት ከስጋው ጦመኛ ነኝ ከመረቁ አውጡልኝ ያለውን አይነት ይመስላል። ትምህርት ቤት የሚሰራው ወጣቶች የሚሰባሰቡት ወላጆች ፍቅር ሲኖራቸው እንጂ በጥል መሃል ሊሆን አይችልም።
ስለሆነም እነዚህን በአድማ የተመረጡ የቦርድ አባላትን በመለማመጥ ሰላም ይፈጠራል ብለን የምናምን ካለን ለነሱ የነገር መግመጃ ጊዜ ከመጨመር በስተቀር መፍተሄ እንደማያመጣ መረዋ ዛሬ ሊያረጋግጥ ይወዳል። ወንድሞቻችንና እህቶቻችን። ሊገል ቆርጦ የመጣን ጠላት ማርኮ አሰሮ ይተወኛል ማለት ሞኝነት ካልሆነም የዋህነት ነው። አንድ ሰው መደራደር የሚችለው እኮ ችግርህ ምንድነው?ብሎ ከሚያዳምጥ ሰው ጋር እንጂ ተባረሃልና የምታመጣውን አያላሁ ከሚል ቡድን ጋር ሊሆን አይችልም።
የደቡብ አፍሪካው ታጋይና የሃይማኖት መሪ ዲዝሞን ቱቱ ሲናገሩ "ነጮች መጽሐፍ ቅዱስ ይዘው መጡ ዓይናችሁን ጨፍኑና ጸልዩ አሉን ጨፍነን መጸለይ ጀመርን ዓይናችንን ስንገልጽ እነሱ መሬቱን ወስደውት እኛ ደግሞ መጽሐፍ ቅዱስ ይዘን ቀረን" ብለው ነበር። እኛም እንዲሁ አይነት እድል ገጠመን ብንል ማጋነን አይሆንም። አቶ አበራ ፊጣ ከመመረጣቸው በፊት "ቤተክርስቲያናችን ገንዘቡ ተዘረፈ የቦርድ አባላት ያለገደብ መብት ተሰጣቸው"ሲሉ እንዳልነበር ዛሬ ታግለው ያላገኙትን ስልጣን ባቌራጭ አገኙና "ሲሾም ያልበላ ........ "ይሉን ጀመር። የቤተክርስቲያንችን ዶክተር ወደ ዳላስ ያስመጧቸውን ሰዎች ውለታ ለመመለስ አድርግ የተባሉትን ሥራ ላይ ለማዋል ጥረው ግረው ምኞታቸው በሥራ ሲተገበር ለማየት እድል ገጠማቸው። የመጨረሻ መደምደሚያቸው ለራሳቸው ሥራ ለምፍጠር ነውና ባረቀቁት ሕጋቸው መሰረት "አንድ የቦርድ ተመራጭ ተቀጣሪ ሆኖ ማገልገል ይችላል የሚለውን" አንቀጽ ተጠቅመው ለመቀጠር ቁጭ ብድግ እያሉ መሆኑን ልንነግራችሁ እንወዳለን። ሌላው የስደት ሲኖዶስ ጉዳይ ነው እሱንም "በአባላት ስብሰባ"ለማስመረጥ እየተሯሯጡ ለመሆኑ ብትጠይቌቸው የሚክዱ አይመስለንም። ያመጧቸውን ሰዎች ውለታ ለመክፈል መብቃት ይኽ ነው።
ትላንትና አቅፈው ደግፈው ዶክተር ለቤተክርስቲያናችን ያሉ ቡድኖች ዛሬ ኧረ በሚካኤል ቢሉ የሚሰማቸው ከቦርዱ ሊያገኙ አልቻሉም። ስለተናደዱባቸው ንዴታቸውን የሚገልጹላቸው ይጠሩበት የነበረበትን የመሃበር ድግስ በመከልከል ሆኖ አይተነዋል። ነገሩ የማር ጋንን አስረክቦ ሰጥቶ ሰፈፍ መከልከል አይነት መሆኑ ነው።
ትላንትና ሲነገራቸው ጆሮ ዳባ ልበስ ያሉት የተፈነቀሉት ሊቀመንበር ዛሬ አንገታቸውን ደፍተው በአቶ አበበ ጤፉ ግልምጫ በአቶ ሙሉ ዓለም እርግጫ እየተናደዱ ለኔም ቀን ይመጣል እያሉ እየጠበቁ ነው።
ዛሬ ያልሆነ ተስፋ በመስጠት ነገሮች ይስተካከላሉ ቁጭ ብላችሁ ጠብቁ ማለትን መስማት የሚፈልግ ሰው ካለ በጣም የዋህ ነው። ማንም ያናግራቸው ማን የቦርዱ አባላት ለምን ምእመን እንዳለ ተገልብጦ አይወጣም እኛ የምንፈልገውን እንጂ የናንተን ፍላጎት አናሟላም ብለው ነግረውናል። ለነገሩማ ባወጡት ሕጋቸው ላይ ቤቱ የወሰነውን ቦርዱ መሻር ይችላል ብለው አውጥተው የለ። ሕጋቸውን እንጂ የአባላትን ሕግማ አሽቀንጥረው ጥለውታል። ትላንት ተው ሲባሉ ይኽ ነገር አደገኛ ነው ሲባሉ ያልሰሙ የትላንትና የቦርድ አባላት ዛሬ ሕጋችን ብለው ተደሰተውበት የነበረው ይኽው ለነሱም ማነቆ ሆኖባቸ ተቸግረዋል። በመሆኑም ትልንት እንዳልነው ዛሬም መፍትሄ ነው ብለን የምናምነው ፦
1 ቦርዱ ከስልጣን እንዲወርድ ሲደረግ
2 መተዳደሪያ ደንባቸን ወደቀድሞው ሲመለስ
3 የሽግግር ኮሚቴ የሚሆኑ የተከበሩ ፈሪሃ እግዚአብሔር ያደረባቸው ሽማሎች ተመልምለው      ለመረከብ ሲበቁ
4 በፈቃዳቸው ካልለቀቁ ባስቸኴይ ተጨማሪ ሕጋዊ እርምጃ መውሰድ ሲቻል
5 የፖለቲካ ድርጅቶች ከቤተክርስቲያናችን ለቀው እንዲወጡ ግልጽና የማያሻማ ጥያቄ ሲቀርብ ይህም ተግባርዊ ሲሆን ብቻ ነው ብለን እናምናለን።
ካልሆነ አሁንም የተቀደደ ከበሮ እየደበደብን ነው ማለት ነው።
ሚካኤል እራሱን ይጠብቃል። ለሚንቁ ብሰለትን:ለሚተበትቡ ምህረትን፡ ለሚጠሉ ፍቅርን፡ ለሚሳደቡ ቅን አንደበትን፡ ለሚዋሹ ምህረትን ያውርድልን።
ክርስቶስ በፍቅር ያሰባስበን።