Tuesday, April 20, 2010

ያረገዘ መውለዱ አይቀር ፳፪

አርግዛለች አሉ ድባብ የፈረንጂ፡
ለኔም ይደርሰኛል አንድ እግር ካንድ እጅ።

ያለው አዝማሪ ምን ችግር አጋጥሞት እንደዚያ እንዳለ ለመተንበይ የሚያስቸግር አይደለም። ዳላስ ላይ ደግሞ ለየት አለና

እደግ እደግ ብለን የተከልነው ቀጋ፡
ዘንበል ዘንበል አለ እኛኑ ሊወጋ።

ብለው የሚያዜሙ አጋጥመውን እንደ ጥንቱ እኛም በፊናችን

አራት እግር አንድ ራስ መንቀል አቅቷችሁ፡
ለብልቦ ለብልቦ አቃጥሎ  ይፍጃችሁ።

ብለን ለሚያንጎራጉሩት መልስ ሰጠናቸው። የእሑዱን የቤተክርስቲያን ስብሰባ እንዴት ነበር? ብለው ለጠየቁን ደግሞ ከዚህ በፊት እትማችን እንዳልነው እኛ ከቁልቌል ወተት አንጠብቅምና ምን ተባለ? ከማለት ይልቅ የሚባለውን ገምግመን አማራጩ ሌላ  መሆን አለበት ካልን ውሎ  አደረ። ስብሰባውን በታዛቢነት ተከታተልን እንጂ ለውጥ ያመጣል ብለን ከጅምሩም አስበነው አናውቅም። በመወያየት ሰላም እንፈጥራለን ይሉ የነበሩ ግለሰቦች በደረሰባቸው ተናደው፡ በሁኔታው ተበሳጭተው ስብሰባውን እየለቀቁ ሲወጡ ስናይ ያልነው ተፈጻሚነት አገኘ አልን እንጂ ምነው? በደህና  አላልንም። ይህ ገርሞን ሳያበቃ "፳ ዓመት የደከምኩበት ቤተክርስቲያን የበሩ ቁልፍ ተነፈግኝ ካሁን በኋላ ስብሰባ ውስጥ አታዩኝም " ብለው እንባ  እየተናነቃቸው ለአባላት አቤቱታቸውን ያቀረቡት የቀድሞው የቤተክርስቲያኑ ያስተዳደር ቦርድ ሊቀመንበር የነበሩት ግለሰብ ስብሰባውን እረግጠው ሲወጡ የተከተሏቸው አንድ የወልቃይት እናት ብቻ እንደነበሩ ስንመለከት ደግሞ   "ሲያልቅ አያምር በሰፈሩት ቁና ........" ማለታችን አልቀረም። የብዙ ጊዜ ጔደኛቸውና የስትራተጂ አማካሪያቸው እንኴን አልተከተሏቸውም። አይገርማችሁም? 

"እኔ ገንዘብ ባይኖረኝም የሰላም እንቅልፍ እተኛለሁ"  ያሉት ዶክተር ማ እንቅልፍ እንደተነሳ  ባይናገሩም የተረበሻችሁ አላችሁ ለማለትና በአሽሙር ግለሰቦችን ለመልከፍ  የተጠቀሙበት እንደነበረ  ለመገመት አልተቸገርንም። ያም ሆነ ይህ ስብሰባው አጣሪ ኮሚቴው እየፈራና እየቸረ ያቀረበው ገለጻ ሙሉ በሙሉ ሳይሰማ የስብሰባው ፍጻሜ ሆነ። የአጣሪው ኮሚቴ አባል የሆኑት የሁለት ልጆች እናት እንዳይናገሩ መብታቸውን የከለከሏቸው የቅርብ ጔደኛቸው የነበሩ ግለሰብ መሆናቸውን ስናይ እሳቸው ካዘኑት በላይ አዘንን።  ምነው ወንድሜ ምን ነካዎ  ብንላቸው ደስ ባለን ነበር። ነገር ግን አናንተ እነማን ናችሁ ተብሎ ድብድብ ቢነሳስ ብለን ፈራን። ዘንድሮ  ደግሞ የፈራ የእናቱ ልጅ ነው የሚለውን የጥንቱን አባባል መለስ ብለን ማሰብ ወደናል። ቤተክርስቲያናችን የደረሰበት እጣ ከሌላው ቦታ  የተለየ  አይደለም። አሁንም ፖለቲካና እምነት የተቀላቀለባቸው የፖለቲካ  መስመራቸው ግብ አልመታ ሲል በጸሎት እንደመለመን አርፎ የተቀመጠውን አማኝ በመበታተን ሲከፋው ያምጻል ግራ  ሲጋባ ከኛ ጎን ይሰለፋል ብለው የሚያልሙ ካልሆነም ከተበተነ የሚታፈስ አይጠፋም ብለው የሚዘገን የሚጠብቁ ግለሰቦች ሕልም እንደሆነ ከተገነዘብን እንደ ሰነበትን ደጋግመንም የተናገርን ይመስለናል። ሲኖዶስን እንደጠላት መፈረጅ አይደለም የኦርቶዶክስ እምነት እንዴት ቢከለስ ፈረንጅኛ ቅርጽ ይኖረዋል ብለው የሚመኙ ቡድኖች የሚቀምሩት ለመሆኑም ሂደቱን በመያት መናገር ይቻላል እንላለን። ለምን ግለሰቦች ያለውን ችግር ለመፍታት ከመሞከር ይልቅ ዝምታን ወደዱ?  ብለን ስንጠይቅ ቀልደኛው ባልደረባችን "አሁንስ እነሱም እንዳይውጣባቸው የሚፈሩት ነገር ያለ ይመስላል"  ብሎን አረፈ ። ለጥርጣሬው መንደረደሪያ ይኑረው እንጂ መረጃ  እንደሌለው ይገባናል።

ባለፈው ስብሰባ የታዘብነው ሌላ ነገር ቢኖር ገንዘብ ጠፋ  አልጠፋ ለማለት ሁሉንም የምንፈልገውን ዶሴዎች ቦርዱ እንድናይ እድል አልሰጠንም ሆኖም በጥቅሉ የጠፋ  ገንዘብ የለም ብለው ሁኔታውን እያብራሩ   ባሉበት  ወቅት ከዚህ ውጭ መናገር አትችሉም ገንዘብ አልጠፋም ብላችኋል በቃ አትናገሩም ብለው የሚያዋክቧቸውን ግለሰቦች ስንመለከት ነው። ትላንት ባገራችን እናትና  አባት ይጋደል የነበረበትን ሁኔታ  አስታወሰን። የተናጋሪዎቹን መብት ይጋፉ የነበሩት ቤተዘመዶች ነበሩና። ለካ እምነትም ፖለቲካ  ነው ብሎ የኔ ቢጤ ግለሰብ ቢወናበድ ምን ይገርመናል። ትላንት የውሸት መታወቂያ  አንግቶ ቤቱን የለቀቀ ስደተኛ ተጋዳይ ቁርባንን እንደመሸሸጊያ እያደረገው ይሆን?  ያለን ሌላው ግለሰብ አፍ አፉን አልነው እንጂ መንደርደሪያ እንደነበረው የሚክድ ከመሃከላችን አንዳችም ግለስብ አልነበረም።

ውድ አንባብያን ባለፈው የነበረው ስብሰባ  ያናደዳቸው ግለሰቦች ስብሰባውን እየረገጡ ሲወጡ ይውጡ ተዋቸው ይሉ የነበሩ ግለሰቦች ያላወቁት ነገር ለደስታ አይደለም ለሐዘንም ሰው እንደሚያስፈልግ ነው። 30 ዓመት በፖለቲካ ሕብረተሰቡን ማሰባሰብ ያልቻለ ተቃዋሚም ይሁን ደጋፊ የፖለቲካ  ቡድን ሰውን በማለያየት ወደ ስልጣን መምጣት ይቻላል ብሎ  የሚያስብ ከሆነ ለሱ "መጽሐፍ ቅዱስ"  ሳይሆን  መጽሐፍ ገላጭ ሊያስፈልገው ነው።

ለማንኛውም በውይይት መፈታት ይቻላል ብላችሁ ያለፈውን ቀን ጠብቃችሁ በውጤቱ የተናደዳችሁ አማንያን ልታደርጉ የምትችሉት ነገር ቢኖር ተነስታችሁ በሕግ መታገል ብቻ ይሆናል ብለን እናምናለን። በፍርድ ቤት  ወሳኔ አንድ መሆን አይቻልም ብንልም ያለው አማራጭ እየጠበበ ምን ይሆናሉ? አሸነፍናቸው ገደል ይግቡ የሚሉትን ግለሰቦች በውይይት ማሳመን አዳጋች ነውና።  የፖለቲካ  አመለከታታችሁ ከኛ ከተለየ እናባርራችኋለን ብለው እያባረሩ ያሉትን ገንዘብ ሳይከፍሉ ገንዘብ የሚቆጥሩትን ቡድኖች መቌቌሚያ  ሌላ  መንገድ ይኖራል ብለን ማመን አቁመናልና። የተለያዩ  ሽማግሌዎች የጀመሩት የማስማማት ጥረት የት እንደደረስ ባናውቅም ካሁን በኋላ  አክብረው ያናግሯቸዋል ብሎ  የሚጠብቅ ካለ የዋህ ብቻ ነው እንላለን። ውድ ወንድሞች ለመብት መታገል አኩሪ ነው። እበላ ባይ መሆን ግን አንድም ክርስቲያናዊ ካልሆነም ፖለቲካዊ ካልያም ሰላማዊ አያደርግም። በመፍራት ሰላም አይመጣም ሰላም በእምነትና በትግል እንጂ። የሚፈራውስ ማን ነው? የሚፈራውስ ለምን? ማለት ደግሞ ለእውነታው መንገድ ይቀዳል። እኔ  በደህና  ግዜ ተምሬ የገንዘብ ችግር የለብኝም ያሉት ግለሰብ የገንዘብ ሳይሆን የእምነት ችግር እንዳለባቸው በግልጽ ይፋ  አደረጉት "ሃብታም ይጸድቃል ከማለት ይልቅ ግመል .............."  ያስታውሷል። እንካ  ስላንቲያ  ውስጥ መግባት ደግሞ የእልፍኝ ሳይሆን የማድቤት ያረገዋልና ሳንናገር እንለፈው።

ወንድሞችና እህቶች ዲያብሎስም ባንድ ወቅት መልአክ እንደነበረ  አንርሳ።
 መልከም ሰንብቱ።